07/04/2026
አዳዲስ የኢኮ ቱሪዝም ስፍራዎችን ማስተዋወቅ ለዘርፉ ዕድገት የጎላ ፋይዳ እንዳለዉ ተጠቆመ
ማህበረሰብ ተኮር የሆኑ አዳዲስ የኢኮ ቱሪዝም ስፍራዎችን የማስተዋወቅ መርሃ ግብር በአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ጫሞ ካምፖስ ተካሂዷል።
በመድረኩ በቋንቋና ባህል ላይ መሰረት ያደረገ "ኢኮ ቱሪዝም" የማስተዋወቅ ፕሮጀክት ቀርቧል።
የአርባምንጭ ዩኒቨርሲቲ የምርምር ኤክስኪዩቲቭ ዳይሬክተር ዶ/ር ተስፋዬ ሀብተማሪያም በወቅቱ እንዳሉት፣ ተቋሙ ለማህበረሰብ ተኮር ስራዎችን ትኩረት መስጠቱን ጠቁመዋል።
የዱቡሻ ስርዓትን በዩነስኮ ለማስመዝገብ በአምስት ቋንቋዎች ላይ መሰረት ያደረገ ጥናትና ምርምር እያካሄደ መሆኑን ለአብነት ጠቅሰዋል፡፡
በዞኑና አከባቢዉ የሚገኙ የቱሪስት መዳረሻ ስፍራዎችን ለጎብኚዎች በቀላሉ ተደራሽ ለማድረግ የሚያስችል የ"ማፕ ዴስቴሽን አፕሊከሽን" ስራ በማጠናቀቅ ላይ እንደሚገኝ ጠቅሰዋል።
የአከባቢዉን የቱሪዝም መዳረሻነት እና አቅም ይበልጥ ለማሳደግ የጋራ ርብርብ እንደሚያስፈልግ ዶ/ር ተስፋዬ አሳስበዋል።
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ቱሪዝም ቢሮ የቱሪዝም መስህብ ጥናት ልማትና ጥበቃ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ አብርሃም አለሙ በበኩላቸዉ፣ በክልሉ ያሉ ባህላዊ ዕሴቶችን በማልማት ፣በመጠበቅና በማስተዋወቅ ረገድ ሰፊ ስራዎች እየተሰሩ ነዉ ብለዋል።
ለህብረተሰቡ ወቅቱ የሚፈልገዉን አገልግሎት ለመስጠት ከዩኒቨርሲቲዎች ጋር በጋራ መስራት እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል።
ቅርሶቻችን ካሉባቸው ችግር ለማዉጣት ሳይንሳዊ አሰራሮች መከተል እንደሚያስፈልግም ጠቁመዋል።
በጋሞ ዞን ቱሪዝም መምሪያ የቱሪስት መስህቦች አገልግሎቶች ልማት አስተባባሪ አቶ ገመቹ ቡልቡላ ፕሮጀክቱ በስፋት ያልተዳሰሱ የቱሪስት ቦታዎች ለማስተዋወቅና ለማልማት ያግዛል ብለዋል፡፡
የአከባቢዉ ማህበረሰብና ወጣቶች የኢኮኖሚ አቅማ ለማሳደግና ለስራ ዕድል ፕሮጀክቱ የላቀ አስተዋጽኦ እንዳለው አመላክተዋል፡፡
በተለያየ መንገድ ፕሮጀክቱን እየደገፈ ያለዉን አርባምንጭ ዩኒቨርሲቲም አመስግነዋል፡፡
አክለዉም በዞኑ የሚገኙ የመስህብ ስፍራዎችን ማልማትና ማስተዋወቅ የሁሉንም ርብርብ ይጠይቃል ብለዋል።
የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ መምህርና ተመራማሪ እንዲሁም የፕሮጀክቱ አስተባባሪ ዳመነ ቦጋለ እንደገለጹት፣ ዞኑ በርካታ የቱሪስት ስፍራዎች ያሉት መሆኑን ጠቁመዉ፣ ፕሮጀክቱ ቱሪዝም ዘርፍ ማህበረሰቡን ተጠቃሚ ማድረግ የሚያስችል ነዉ ብለዋል።
አርባ ምንጭ፡- መጋቢት 29/2018 ዓ.ም(ጋሞ ቴሌቪዥን)