05/09/2026
የሕዝብና የመንግሥትን ሀብት ከሙስናና ከምዝበራ ለመጠበቅ ችግሮችን በጊዜ ለመለየትና በሕግ ማስጠየቅ የሚያስችል ትክክለኛ መረጃ የመያዝ ስራ በልዩ ትኩረት እየተሰራ መሆኑ ተገለፀ
ነሐሴ 30/2018ዓ.ም
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ሥነ-ምግባርና ፀረ-ሙስና ኮሚሽን ከሥነ-ምግባር መከታተያ ክፍሎችና ከተቋሙ ሠራተኞች ጋር መክሯል።
የኮሚሽኑ ኮሚሽነር አቶ ተካልኝ ጋሎ እንደገለጹት የሕዝብና የመንግሥትን ሀብት ከሙስናና ከምዝበራ ለመጠበቅ ችግሮችን በጊዜ ለመለየትና በሕግ ማስጠየቅ የሚያስችል ትክክለኛ መረጃ የመያዝ ስራ በልዩ ትኩረት እየተሰራ መሆኑ ገልጸዋል ።
ትክክለኛ መረጃን በአግባቡ ማደራጀትና ሚስጥራዊነቱን መጠበቅ የሙስና ጉዳዮችን በሕግ ለማስጠየቅ ወሳኝ መሆኑንም አሳውቀዋል።
አንድ ድርጊት አጠራጣሪ መሆኑን ማወቅ ብቻ በቂ አለመሆኑን የጠቆሙት ኮሚሽነሩ ድርጊቱ ሙስና መሆኑን በሕግ ፊት ለማረጋገጥ የሚችል ግልጽ፣ ተአማኒና በአግባቡ የተደራጀ ማስረጃ መያዝ ተገቢ እንደሆነ አመላክተዋል።
የጠራ መረጃ ለኮሚሽኑ ትልቅ መሣሪያ ነው ያሉት ኮሚሽነር ተካልኝ፣ ከኮሚሽኑ ጀምሮ እስከ ታችኛው መዋቅር ድረስ የመረጃ አያያዝና አጠቃቀም ሥርዓትን ለማጠናከር የጋራ ጥረት እንደሚያስፈልግ አመልክተዋል።
በተጨማሪም ትክክለኛ መረጃ ተይዞ እንኳን በአግባቡ ካልተደራጀና ሚስጥራዊነቱ ካልተጠበቀ የሕግ ሂደቱን ሊያደናቅፍ እንደሚችል ጠቁመው፣ መረጃን በማደራጀትና በመጠበቅ የሙስና ወንጀል ተጠርጣሪዎች ሕጋዊ ክፍተት እንዳያገኙ መሥራት እንደሚገባ አስረድተዋል።
የክልሉ ሥነ-ምግባርና ፀረ-ሙስና ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነርና የሙስና መከላከል ዘርፍ ኃላፊ ኮሚሽነር አማኑኤል አብደላ በበኩላቸው፣ የሙስና መከላከል ሥራን ለማጠናከር መረጃን በሥርዓት መሰብሰብ፣ ማደራጀትና መተንተን የሚያስችል አቅም መገንባት እንደሚገባ ገልጸዋል።
የመረጃ ሥርዓቶችን ዲጂታል ማድረግ፣ የተለያዩ የመረጃ ምንጮችን ማስተሳሰርና የመረጃ ጥራትን ማረጋገጥ የሙስና ስጋቶችን በተሻለ ሁኔታ ለመለየትና ተገቢውን የመከላከል እርምጃ ለመውሰድ የሚያግዝ መሆኑንም አስታውቀዋል።
የመድረኩ ተሳታፊዎች በሰጡት አስተያየት መረጃን በጥራት ሰብስቦ በአግባቡ ማደራጀትና ለውሳኔ አሰጣጥ ማዋል በሙስና ትግል ውጤታማነት ላይ ያለውን ሚና በተሻለ መልኩ መገንዘባቸውን ገልጸዋል።
በመድረኩ የተገኘውን እውቀት ወደ ተግባር በመቀየር የመረጃ ጥራትንና የትንተና አቅምን ለማጎልበት፣ በተለይም መረጃን ለሕግ ማስከበርና ለውሳኔ አሰጣጥ በተገቢው ሁኔታ ለመጠቀም በትኩረት እንደሚሠሩ አስታውቀዋል።