31/08/2026
ርዕሰ መስተዳድር አቶ አሻደሊ ሀሰን በኢትዮጵያ የዩኒሴፍ የፕሮግራም ዘርፍ ምክትል ተወካይ ሚስተር አርጃን ደ ዋግት ጋር ተወያዩ
*************
(አሶሳ፣ ነሃሴ 25/2018 ዓ/ም) የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አሻደሊ ሀሰን በኢትዮጵያ የዩኒሴፍ የፕሮግራም ዘርፍ ምክትል ተወካይ ሚስተር አርጃን ደ ዋግት የተመራ ልዑክ ጋር በጽህፈት ቤታቸው ተቀብለው ተወያዩ።
በውይይታቸውም በክልሉ በዩኒሴፍ ድጋፍ የተሰሩ ፕሮጀክቶች የስራ አፈጻጸም ያለበት ሁኔታና የክልሉን ህዝብ የልማት ፍላጎቶች ከማሟላት አንጻር እያደረገ ያለውን አበርክቶ እንዲሁም በቀጣይ ድጋፍና እገዛ የሚፈልጉ ወሳኝ ጉዳዮችን የሚያመላክት ሰነድ በክልሉ ፋይናንስ ቢሮ ኃላፊ አቶ ዚያድ አብዱላሂ በኩል ቀርቧል።
የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ አሻደሊ ሀሰን ዩኒሴፍ ኢትዮጵያ ለክልሉ ህዝብ እያደረገ ላለው ዘርፈ ብዙ አበርክቶ አመስግነዋል።
አቶ አሻድሊ አክለውም ክልሉ በርካታ ስደተኞችን ተቀብሎ እያስተናገደ መሆኑን በመግለጽ በዚህም ምክንያት የጤና ተቋማትን፣ የንጹህ መጠጥ ውሃ ፣ የትምህርትና ሌሎች ማህበራዊ አገልግሎት ሰጭ ተቋማትን ተጋርቶ እየተጠቀመ በመሆኑ በክልሉ እና በተቃባዩ ማህበረሰብ ዘንድ ተጽዕኖ እያሳደረ እንደሚገኝ በመጠቆም የአጋር አካላትን ትኩረትና ያልተቋረጠ እገዛ እንደሚፈልግ ተናግረዋል።
የዩኒሴፍ ኢትዮጵያ የፕሮግራም ዘርፍ ምክትል ተወካይ ሚስተር አርጃን ደ ዋግት በበኩላቸው ለተደረገላቸው አቀባበልና ስለቀረበላቸው አጠቃላይ ገለጻ አመስግነው በተለይ የክልሉ መንግስትና ህዝብ ስደተኞችን ተቀብሎ እያስተናገደበት ያለውን መንገድ አድንቀዋል።
ዩኒሴፍ ኢትዮጵያ ለክልሉ ህዝብ የሚያደርገውን ሁለንተናዊ ድጋፍና እገዛ አጠናክሮ እንደሚቀጥልም ተናግረዋል።
መረጃው፦ የክልሉ ፕሬዚዳንት ጽ/ቤት ነው