04/06/2026
7ኛው ጠቅላላ ምርጫ በከተማ ደረጃ ፍፁም ሰላማዊ፣ ተዓማኒነት ያለውና ደህንነቱ የተጠበቀ ሆኖ በመጠናቀቁ የምስጋና መድረክ ተካሄደ።
የሐዋሳ ከተማ አስተዳደር 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ በከተማ ደረጃ ፍፁም ሰላማዊ፣ ተዓማኒነት ያለውና ደህንነቱ የተጠበቀ ሆኖ በመጠናቀቁ ለከተማዋ አመራር እና የፀጥታ አካላት የምስጋና መድረክ አካሄደ።
የከተማው አጠቃላይ አመራርና የፀጥታ መዋቅሩ ቁርጠኝነትና ቅንጅት ለምርጫው ስኬታማነት ፍትሃዊ፣ ገለልተኛ ፣ነፃና ታዓማኒነት ያለው ምርጫ ለማካሄድ እጀ ንፁህና ልበ ንፁህ ሆኖ ማገልገሉና የተሰጠውን አቅጣጫ ተቀብሎ የመራበት አግባብ ለምርጫው ውጤታማነት ጉልህ አስተዋጽኦ ማበርከቱም ከመድረኩ ተመላክቷል።
7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ታሪካዊ ምርጫ መሆኑን መድረኩን የመሩት የሐዋሳ ከተማ ከንቲባ ጥራቱ በየነ ገልፀው ለምርጫው ሰላማዊነትና ዴሞክራሲያዊነት ለሰሩና በምርጫው ሂደት ለተሳተፉ ለሁሉም አካላት የሚያኮራ ውጤት የተመዘገበበት ምርጫ መሆኑን አክለዋል።
የምርጫው ስኬት እንደተጠበቀ ሆኖ በከተማዋ በበጀት ዓማቱ የተጀመሩ የልማት ስራዎች በተያዘላቸው የጊዜ እና የዲዛይን ጥራት መሰረት ተጠናቀው ተገቢውን አገልግሎት መስጠት እንዲችሉ እና በድል ለማጠናቀቅ በላቀ ቁርጠኝነት መስራት እንደሚገባም ከንቲባው አያይዘው ገልፀዋል።
የሐዋሳ ከተማ ብልፅግና ፓርቲ ዋና ቅ/ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ማራዶና ዘለቀ በበኩላቸው ነዋሪው የተለያዩ ጫናዎችን ተቋቁሞ በምርጫው በነቂስ በመሳተፍ ዴሞክራሲያዊ መብቱን መጠቀሙ የከተማው ነዋሪ ሰላም ወዳድነት አንዱ ማሳያ መሆኑን ገልፀው በቅንጅትና በጋራ ከተሰራ በምርጫው የተመዘገበው ውጤት ማንኛውንም ስራ በብቃት ማሳካት እንደሚቻል አመላካች ነውም ብለዋል።
በመድረኩ በክብር እንግድነት የተገኙት የሲዳማ ክልል ከተማና መሰረተልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ብሩክ ሰለሞን በነዋሪው ሰላም ወዳድነትና የጎለበተ ዴሞክራሲያዊ አስተሳሰብ እንዲሁም በምርጫ ስራው በአመራሩና የፀጥታ አካላት ገለልተኛ፣ ፍትሃዊና ነፃ ሆኖ ማገልገል ምርጫው ፍፁም ሰላማዊና ደህንነቱ የተጠበቀ ሆኖ መጠናቀቁን ገልፀዋል።
ዘገባው የሐ/ከ/አስ/የመ/ኮ/ጉ/መምሪያ ነው