25/08/2026
የክልሉ ፋይናንስ ቢሮ ከገንዘብ ሚኒስቴርና ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ፋይናንስ ቢሮ ጋር በሪፎርም ትግበራ ዙሪያ የልምድ ልውውጥ አካሄደ
ነሐሴ 18/2018 ዓ.ም
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ፋይናንስ ቢሮ፥ የፋይናንስ ሴክተር የመንግሥት አገልግሎትና አስተዳደር ሪፎርም የዝግጅት ምዕራፍ ትግበራን አስመልክቶ ከገንዘብ ሚኒስቴርና ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ፋይናንስ ቢሮ ጋር የልምድ ልውውጥና የምክክር መድረክ አካሂዷል።
በመድረኩ የሪፎርሙ የዝግጅት ምዕራፍ ትግበራ አፈጻጸም፣ በዕቅድ መሠረት የተከናወኑ ተግባራት፣ የተመዘገቡ ውጤቶችና በትግበራ ሂደቱ የተለዩ ተግዳሮቶች በስፋት ተገምግመዋል።
ከገንዘብ ሚኒስቴርና ከአዲስ አበባ ፋይናንስ ቢሮ የተገኙ ተሞክሮዎችም ቀርበው፣ በተለይም የሪፎርሙን ትግበራ በተሻለ አቅም ለማስፈጸም የሚያስችሉ የአሠራር አቅጣጫዎች ላይ ሰፊ ምክክር ተደርጓል።
የሪፎርሙን የትግበራ አቅም ማጠናከር፣ የሥራ ሂደቶችን ማሻሻል፣ ተቋማዊ አሠራሮችን ማዘመንና ቀልጣፋና ውጤታማ የመንግሥት አገልግሎትን ማረጋገጥ በሚቻልባቸው አግባቦች ላይም ትኩረት ተሰጥቷል።
የልምድ ልውውጡ በፋይናንስ ሴክተሩ የሚከናወኑ የሪፎርም ሥራዎችን በተቀናጀና በተጠናከረ መልኩ ለማስቀጠል፣ የአሠራር ሥርዓቶችን ለማዘመንና የተቋሙን የአፈጻጸም አቅም ለማሳደግ ጠቃሚ ግብዓት መሆኑ ተገልጿል።
በተጨማሪም የሪፎርሙ ትግበራ የመንግሥት አሠራርን ይበልጥ ቀልጣፋ፣ ውጤታማና ተጠያቂ በማድረግ ለዜጎች የሚሰጠውን የመንግሥት አገልግሎት ጥራት ለማሻሻል የሚያግዝ መሆኑ ተመልክቷል።
በመድረኩ የተጋሩ ልምዶችና ተሞክሮዎች፣ እንዲሁም የተነሱ ሀሳቦች፣ የፋይናንስ ሴክተሩን የሪፎርም ሥራ በቀጣይ በተጠናከረ አግባብ ለመምራትና የታቀዱ ውጤቶችን ለማስመዝገብ ወሳኝ ግብዓት እንደሚሆኑ ተጠቁሟል።