30/08/2026
በመካነ ኢየሱስ ከተማ አሥተዳደር ከ900 በላይ ለሚሆኑ ተማሪዎች የትምህርት ቁሳቁስ ድጋፍ ተደረገ።
በደቡብ ጎንደር ዞን በመካነ ኢየሱስ ከተማ አስተዳደር "በትምህርት ቁሳቁስ እጥረት ምክንያት አንድም ተማሪ ከትምህርት ገበታ መቅረት የለበትም" በሚል መሪ ቃል በክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት የተሰበሰበ የትምህርት ቁሳቁስ ድጋፍ ለሚሹ ተማሪዎች ተሰራጭቷል።
በበጎ ፈቃድ የተሰበሰበው የትምህርት ቁሳቁሱ ከከተማዋ ነዋሪዎች ከተለያዩ ተቋማት ድርጅቶችና ባለሀብቶች የተገኘ መሆኑ ተገልጿል።
ድጋፉ በገንዘብ ሲተመን ከ600 ሺህ በላይ ብር የሚያወጣ ሲሆን ከ800 ደርዘን በላይ ደብተር እና ከ130 ባኮ በላይ እስክሪብቶ ነው።
የተሰበሰበው የትምህርት ቁሳቁስም ድጋፍ ለሚያስፈልጋቸው ከ900 በላይ ለሚሆኑ የነገ ሀገር ተረካቢ ተማሪዎች ስርጭት ተደርጓል።
በትምህርት ቁሳቁስ ስርጭቱ ላይ ተገኝተው ለተማሪዎች ድጋፉን ያሰራጩት የከተማ አስተዳደሩ ምክትል ከንቲባና የንግድ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ዳንኤል ሙሉአለም እንደገለጹት ድጋፉ የልጆችን የትምህርት ቁሳቁስ ችግር ከመቅረፉ ባሻገር ዛሬ ከሚያዩት ማህበራዊ ተግባር መረዳዳትንና መተጋገዝን ተምረው እንዲያድጉ ትልቅ አስተዋጽኦ አለው ብለዋል።
የከተማ አስተዳደሩ የብልፅግና ፓርቲ የአቅም ግንባታና የፖለቲካ ዘርፍ ኃላፊ አቶ መኳንንት ታደሰ በበኩላቸው በዚህ ክረምት የቤት እድሳት የእህል ድጋፍና የማዕድ ማጋራትን ጨምሮ በርካታ አቅመ ደካሞችን የደገፉ ስራዎች መከናወናቸውን ገልጸዋል።
በስርጭት መርሃ ግብሩ የከተማና የቀበሌ አመራሮች፣ ተማሪዎች እንዲሁም የተማሪ ወላጆች በቦታው ተገኝተዋል።
"የመረዳዳት እና የበጎ ፈቃድ ባህላችን ይለምልም!"