06/09/2026
🌱 እመርታ ለዘላቂ ከፍታ!
የጷጉሜ -1 የእመርታ ቀን በወልድያ ከተማ ተከበረ!
የጷጉሜ -1 የእመርታ ቀን በወልድያ ከተማ አስተዳደር ግብርና መምሪያ አስተባባሪነት በተለያዩ የግብርና፣ የእንስሳትና የአሳ ሀብት ልማት እንዲሁም የኢንዱስትሪ ስራዎችን በማሳየት ተከብሯል!
በዕለቱ የግብርና መምሪያ ኃላፊ ወ/ሮ ደስታ ሞላ እንደገለጹት፣ ግብርና የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈ ለኢንዱስትሪ ዘርፍ ግብዓት የሚያቀርብ የኢኮኖሚ መሠረት ነው።
በዘርፉ የምርታማነት ማሳደግ፣ የአትክልትና ፍራፍሬ ምርትን ማስፋፋት፣ እሴት ጨምሮ ማቀነባበርና ለኢንዱስትሪ የሚሆን ጥሬ ዕቃ ማቅረብ ላይ ትኩረት ተደርጎ ይሰራልም ብለዋል።
የከተማ አስተዳደሩ የፖለቲካና አቅም ግንባታ ዘርፍ ኃላፊ ክብርት ወ/ሮ አስናቀች ኃይሌ በበኩላቸው፣ የእመርታ ቀን ያለፈውን የምንገመግምበት፣ የተሳካውን የምናጠናክርበት፣ ያልተሳካውን የምንለይበትና ለቀጣይ የተሻለ የልማት ጉዞ የምንዘጋጅበት ቀን መሆኑን ገልጸዋል።
በዕለቱ ከተጎበኙ የልማት ቦታዎች መካከል የደሳለኝ ኢንዱስትሪያል ኢንጂነሪንግ አንዱ ሲሆን፣ የድርጅቱ ባለቤት አቶ ደሳለኝ ፈንታው በፋብሪካቸው የኮሪደር ልማት አካል የሆኑ ስማርት ፖሎችን፣ተንጠልጣይ ድልድዮችን እያመረቱ ለተለያዩ ዘኖች እና ወረዳዎች ተደራሽ እያደረጉ መሆኑን ገልጸዋል።
በቀጣይ የብድርና የፋይናንስ ድጋፍ ከተመቻቸላቸው የማምረት አቅማቸውን በማስፋፋት ከዚህ በበለጠ ስፋት ለከተማው የልማት ስራዎች ግብዓት ለማቅረብ ዝግጁ መሆናቸውን ጠቁመዋል።
በተመሳሳይ የከተማ አስተዳደሩ እንስሳትና አሳ ሀብት ልማት መምሪያ በእንስሳት ልማት እና በአሳ እርባታ ዘርፍ የተጀመሩ ስራዎችን አስተዋውቋል።
የመምሪያዉ ኃላፊ አቶ በላይ ገሰሰ በበኩላቸዉ በዘርፉ የተጀማመሩት ስራዎች አይን ገላጭ ሲሆኑ በዚህ በጀት አመት በስፋት ወደ ስራ የሚገባበት ዘርፍ እንደሆነ ገልጸዋል።
በአትክልትና ፍራፍሬ፣ በአሳ እርባታ እና በፍየል ማድለብ ስራዎች የተሰማሩት አቶ አበበ ግርማይ በበኩላቸው፣በዚህ ስራ በመሰማራታቸዉ የራሳቸዉን ፍላጎት ከማሟላት ባሻገር የገቢ ምንጫቸውን ማስፋፋት እንደቻሉ ገልጸው፣ የግብርናዉ ዘርፍ በተገቢ መንገድ ድጋፍ ካገኘ እና በተደራጀ አሰራር ከተመራ ለስራ ዕድል ፈጠራና ለገቢ ማስገኛ ሰፊ አቅም እንዳለው አስረድተዋል።
እመርታ የስራ ውጤት ብቻ ሳይሆን፣ የቀጣይ ዕድገት መነሻ ነው