23/05/2026
በማዕከላዊ ጎንደር ዞን የሚንቀሳቀሱ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች የሚከናወኑ የልማት ስራዎችን በመከታተል እና በመደገፍ ውጤታማ ማድረግ እንደሚገባ ተገለጸ
የማዕከላዊ ጎንደር ዞን ገንዘብ መምሪያ የመንግስትንና የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች የምክክር መድረክ አዘጋጅቷል።
በዕለቱ ተገኝተው የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ አወቀ አስፈሬ፥ የልማት ድርጅቶች በዞኑ ዘርፈብዙ ስራዎችን እያከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል።
ለዚህም የህብረተቡን ችግሮች ለመፍታት የሚያከናውኗቸውን የልማት ተግባራት በሚገባ መከታተል እና መደገፍ እንደሚገባ አስገንዝበዋል፡፡
በዞኑ የተያዙ የልማት እቅዶች በተያዘላቸው ጊዜ እንዲጠናቀቁ የጋራ ርብርብ ይጠይቃል ያሉት ዋና አስተዳዳሪው ባለድርሻ አካላት በእነዚሁ ድርጅቶች የሚከናወኑ የልማት ስራዎችን በመከታተል እና በመደገፍ ውጤታማ ማድረግ እንደሚጠበቅባቸውም ተናግረዋል፡፡
የመንግስት እና የሲቪል ማህበራት ጥምረት የህዝብን የልማት እና የመልካም አስተዳደር ጥያቄ መመለስና ፍትሃዊ ተጠቃሚነት ማስፈን እንደሚያስችል ጠቁመው፤ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ድጋፍ ሊጠናከር እንደሚገባም አክለዋል፡፡
የዞኑ ገንዘብ መምሪያ ኃላፊ ወ/ሮ ሰላማዊት ነጋ በበኩላቸው በተቋቋመው አዋጅ መሠረት ተግባራዊ ተደርጎ በየጊዜው የጋራ ግምገማ መደረጉን አንስተዋል።
በዞኑ በዘንድሮው በጀት ዓመት 26 የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ሁለት ነጥብ አንድ ቢሊዮን በሚጠጋ ብር 28 የልማት ፕሮጀክቶች እያከናወኑ ይገኛሉ ብለዋል፡፡
ጤና፣ ትምህርት፣ ንጹህ የመጠጥ ውሃ አቅርቦት ማስፋፋት እና የሴቶች እና ህጻናት ተጠቃሚነት ማጎልበት ድርጅቶቹ የዞኑን መንግስት ጥረት እየደገፉ ከሚገኙባቸው ዘርፎች መካከል እንደሆኑ አስረድተዋል፡፡
በዞኑ ስምምነት ወስደው እየተቀሳቀሱ ከሚገኙ 26 የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ውስጥ 15ቱ አገር አቀፍ እና 11ዱ ደግሞ አለምአቀፍ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች እንደሆኑም ታውቋል።
በዚሁ የምክክር መድረክ የተለያዩ የዞኑ ሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች አመራር አባሎች እንዲሁም ጉዳዩ የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል።
ማዕከላዊ ጎንደር ዞን ኮሚዩኒኬሽን