02/09/2026
ተቋማዊ ራስን መፈተሽ ለላቀ የመልካም አስተዳደር ጉዞ !!!
………….27/12/2018………..
ሂላችንም እንደምናውቀው የዘመን መለወጫ በባህላችን የደስታ፣ የአበቦች መታያ፤ ጉም ጭጋጉ ተወግዶ የብርሃን ማብሰሪያ ብቻ አይደለም፤ ይልቁንም እንደ አንድ ተቋም ያለፈውን አካሄድ መዝኖ፣ የተጓዙትን መንገድ ገምግሞና ስህተትን አርሞ ወደ አዲስ ምዕራፍ የሚሸጋገሩበት ታላቅ መንፈሳዊና ማህበራዊ ድልድይ እንጂ።
ለአንድ ግለሰብ ዘመን መለወጥ የዕድሜ ቁጥር መጨመርን ብቻ ሳይሆን የህሊና ምልከታን እንደሚጠይቅ ሁሉ፣ ለአንድ ተቋም ደግሞ የአዲስ ዓመት መባቻ ማለት የመልካም አስተዳደር ጉዞውን ቆም ብሎ የሚፈትሽበት፣ የአገልግሎት ጥራቱን የሚመዝንበት እና የወገኖችን በህግ የተደነገገ መብት ማስከበሩን የሚያረጋግጥበት ተቋማዊ ኦዲት የሚያደርግበት ወርቃማ ወቅት ነው ማለት ይቻላል።
እናም አዲሱን ዓመት በደስታና በአዲስ ተስፋ ለመቀበል ከመሸጋገራችን በፊት፣ ተቋማት “ባለፈው ዓመት ለህዝባችን በመልካም አስተዳደር በኩል ምን ሰራን? የአገልግሎት መስኮቶቻችን ምን ያህል ግልጽና ፍትሃዊ ነበሩ?” ብለው ራስን መጠየቅ ከይስሙላ በዓል አከባበር ይልቅ ዘላቂና እውነተኛ የተቋም ግንባታ መደላደል የተሻ ነው ቢባል ማጋነን አይሆንም።
ተቋማዊ ራስን መፈተሽ (Self-Reflection) ለምን ያስፈልጋል?
በማህበራዊና ፖለቲካዊ ፍልስፍና ታሪክ ውስጥ የመልካም አስተዳደርና የተቋማት ጥራት ያለ አስተዳር ኦዲትና ያለ ተቋማዊ ምርመራ ሊጎለብት እንደማይችል ምሁራን ያስገነዝባሉ። ጥንታዊው ግሪካዊ ፈላስፋ ሶቅራጥስ (Socrates) “ያልተፈተነ ሕይወት ለመኖር ዋጋ የለውም” እንዳለው ሁሉ፣ በዘመናዊ አስተዳደርም “ያልተፈተነና ያልተገመገመ ተቋማዊ አሠራር ለሕዝብ ጠቃሚ አገልግሎት ሊሰጥ አይችልም።”
አንድ ተቋም መልካም አስተዳደርን በጥሩ መሰረት ላይ ለመትከል ከፈለገ፣ ከአዲሱ ዓመት ጩኸትና አቀባበል በፊት የውስጥ አሠራሩን፣ የባለሙያዎቹን ሥነ-ምግባር፣ የቅሬታ አቀራረብ ሥርዓቱን እና ለሴቶች፣ ሕፃናት፣ አረጋውያንና አካል ጉዳተኞች የፈጠረውን ተደራሽነት በጥልቀት ሊመረምር ይገባል ብሎ መናገር ይቻላል።
ታዋቂው የማኔጅመንት መምህር ፒተር ድራከር (Peter Drucker) ሲናገር፡
“የማይለካ ነገርን ማስተዳደር አይቻልም፤ የማይፈተን አሠራር ደግሞ ሊሻሻል አይችልም።” ብሏል፡፡
ስለሆነም ዘመን ከመቀየሩ በፊት የውስጥ አሠራርን፣ የሀብት አጠቃቀምን እና የአገልግሎት እርካታን መለካትና ማወቅ የነገው ስኬት መሰረት እንደሆነ ከግምት ማስገባት ያስፈልጋል።
የመልካም አስተዳደር ምሰሶዎችና የተቋማት ኃላፊነት
መልካም አስተዳደር በወረቀት ላይ የተጻፈ መመሪያ ወይም የቃል ኪዳን ሰነድ ብቻ አይደለም፤ በዕለት ተዕለት አገልግሎት ላይ የሚገለጥ የተቋም መገለጫ እንጂ። የዓለም ባንክና የተባበሩት መንግሥታት የልማት ፕሮግራም (UNDP) የመልካም አስተዳደር መሠረቶች አድርገው የሚያስቀምጧቸው የሚከተሉት ናቸው፡-
1. ሕግን ማክበርና ማስከበር (Rule of Law)
2. ግልጽነት (Transparency)
3. ተጠያቂነት (Accountability)
4. አሳታፊነትና ምላሽ ሰጪነት (Responsiveness & Inclusivity) ናቸው።
የቀድሞው የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ጸሐፊ ኮፊ አናን (Kofi Annan) የመልካም አስተዳደርን አስፈላጊነት ሲገልጹ፡
“መልካም አስተዳደር ምናልባትም ድህነትን ለማስወገድና ልማትን ለማፋጠን የሚረዳው አንድ ዋናውና ወሳኙ መሣሪያ ነው።” ብለው ነበር።
በመሆኑም አዲሱን ዓመት ስንቀበል ተቋማቶቻችንን፡
• ለተገልጋዮች ተገቢውን አገልግሎት ስንሰጥ ነበርን?
• ችግሮቻችን ምን ነበሩ? ጠንካራ ጎናችንስ?
• ተገልጋዩ ስለ 2018 በጀት አመት አገልግሎታችን ምን ይላል?
• ሴቶችና አካል ጉዳተኞች በእኩልነትና ያለ አድልዎ አገልግሎት አግኝተዋል?
• ለአረጋውያንና ሕፃናት የሚገባቸው ልዩ እንክብካቤና ቅድሚያ ተሰጥቷል?
• ተቋማችን የሙስናና የአሠራር ጉድለቶች የጸዳ፣ ግልጽነት ያለው እንዲሆን ምን አደረግን? ወዘተ
ብሎ መጠየቅና የአሠራር ማሻሻያዎችን (Reform) ማቀድ የሁሉም አስተዳዳሪዎችና ሠራተኞች ግዴታ ነው ብሎ መናገር ይቻላል።
አዲሱ ዓመት፡ ለመልካም አስተዳደር የተስፋና የተሐድሶ ምዕራፍ
ዘመን ሲቀየር አሮጌ አስተሳሰብና በደል አብሮ ሊቀየር እንደሚገባ ዕሙን ነው፡፡ በበጀት ዓመቱ የተሰሩ ስህተቶችን መደበቅ ወይም "ባለፈው አልፏል" ብሎ ችላ ማለት መልካም አስተዳደርን አይገነባም። ይልቁንም የተፈጸሙ ጉድለቶችን በግልጽነት በመቀበል፣ ተጠያቂነትን በማረጋገጥና አሠራርን በማዘመን ወደ አዲሱ ዓመት መሸጋገር ተቋማዊ ብስለትን ያሳያልና እንጠቀምበት ለማለት እንወዳለን።
ታላቁ የሰብዓዊ መብት ታጋይ ኔልሰን ማንዴላ (Nelson Mandela) እንዳሉት፡
“ስኬት ማለት ፈጽሞ አለመውደቅ አይደለም፤ ይልቁንም በወደቅን ቁጥር ተነስተን ጉዞአችንን መቀጠል መቻላችን ነው፡፡”
ስለሆነም ተቋማት ባለፈው ዓመት የነበሩባቸውን የመልካም አስተዳደር እክሎች፣ የቢሮክራሲ እንግልቶችና የአገልግሎት መዘግየቶች በግልጽ ገምግመው፣ በአዲሱ ዓመት የተሻለ፣ ቀልጣፋ፣ ፍትሃዊና ለዜጎች ክብር የሚሰጥ አገልግሎት ለመስጠት ራሳቸውን ማዘጋጀት እንዳለባቸው ዛሬ ላይ ቆም ብለው ማሰብ አለባቸው፡፡
አዲሱ ዓመት የጽጌረዳ አበባዎች የሚፈኩበትና አየሩ በበጎ መንፈስ የሚሞላበት ወቅት እንደመሆኑ መጠን፣ የተቋማቶቻችን አሠራርና አገልግሎትም እንደ አዲሱ ዓመት የታደሰና የጠራ እንዲሆን መስራት የአቅዳችን አንዱ አካል ቢሆን መልካም ነው፡፡
ወደ አዲሱ ዓመት ከመሸጋገራችን በፊት አሁኑኑ ቆም ብለን ተቋማችንን እንመርምር! ጉድለቶቻችንን እንረም፤ ስኬቶቻችንን አጠናክረን እንቀጥል! መልካም አስተዳደር በምኞት ሳይሆን በቁርጠኝነት፣ በፍትሃዊነትና በዕለት ተዕለት ተግባር የሚገነባ የህዝብ እምነት መገለጫ ነው። አዲሱ ዓመት የሕግ የበላይነት የሚነግስበት፣ የተጋላጭ ወገኖች መብት የሚከበርበት እና የተቋማት አገልግሎት ለዜጎች እፎይታ የሚሰጥበት የላቀ የመልካም አስተዳደር ዘመን ይሁንልን
ለማለት እንወዳለን!
• ተዘጋጀ በህዝብ ግንኙትና ኮሙኒኬሽን ክፍል
ነሐሴ 27, 2018ዓ/ም
ባህር ዳር