02/06/2026
ይምርሃነ ክርስቶስ
ይምርሃነ ክርስቶስ ከ900 ዓመታት በፊት ከላሊበላ ከተማ 42 ኪ.ሜ ርቀት ላይ በሚገኝ የተራራ ዋሻ ውስጥ የተሰራ እጅግ አስደናቂ ቤተ ክርስቲያን ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያኑ ከዛግዌ ዘመነ መንግስት ስመ ገናና ነገሥታት አንዱ በሆኑት ንጉሥ ወቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ የተሰራው ነው፡፡
የቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን በአሰራር ጥበቡ እጅግ የተለየ ሲሆን ጌጠኛ ድንጋዮች ከላይና ከታች በጥንቃቄ በተጠረቡ ሰፋፊ እንጨቶች የተያያዙና በጠንካራ ኖራ መሰል ማጣበቂያ የተለሰኑ ናቸው፡፡ ወለሉ ጠንካራ በሆነ ጥርብ ድንጋይ የተነጠፈ ሲሆን ታቹ ውሃ(ባህር) ነው፡፡ የጣራው ክፍል ወይም ኮርኒሱ ከእንጨት የተሰራና በመስቀል፣ ፀሐይ፣ ጨረቃና ከዋክብት ስዕሎች የተንቆጠቆጠ ነው፡፡ በልዩ ሁኔታ የተቀረጹ እና በመስቀልና ሐረግ ቅርጻ ቅርጾች የተጌጡ 22 የሚከፈቱ እና 4 የማይከፈቱ በድምሩ 26 መስኮቶችም አሉት፡፡