07/05/2026
በቀሪ 60 ቀናት የበጀት ዓመቱን ገቢ ዕቅድ መቶ በመቶ መጨረስ እና የ2019 ግብ ማስቀመጥ እንደሚገባ ክቡር መንገሻ ፈንታው (ዶ/ር) መምሪያ ሃላፊዎችን አሳሰቡ።
ሚያዝያ 28/2018 ዓ.ም (የአማራ ክልል ገቢዎች ቢሮ) የአማራ ክልል ገቢዎች ቢሮ ሃላፊ ክቡር መንገሻ ፈንታው በቢሮው የዘጠኝ ወራት ዕቅድ አፈጻጸም ግምገማ ላይ ተገኝተው የስራ መመሪያ ሰጥተዋል።
ቢሮው በአራት መድረኮች ያከናወነው የዘጠኝ ወራት ዕቅድ አፈጻጸም መድረክ ጠንካሮችን አሞካሽቶ፣ መካከለኞችን አበረታቶ ዝቅተኞችን ደግሞ ክፍተታቸውን ለይቶ ልዩ ክትትልና ድጋፍ ለማድረግ ስምምነት ላይ ደርሷል።
በ2018 ዓ.ም በጀት ዓመት ቀሪ የግንቦትና የሰኔ ወር 60 ቀናት የገቢ ዕቅዱ መቶ በመቶ የሚጠቃለልበት የማጠቃለያ ምዕራፍ እንዲሁም ለ2019 ዓ.ም አዲስ በጀት ዓመት ግብር ለመሰብሰብ የሚያስችል የዝግጅት ምዕራፍ በሚል ተወስኗል።
መምሪያ ሃላፊዎች “ጨርሶ መጀመር” በሚል መርህ የስራ አመራር ክህሎታቸውን ተጠቅመው በቀሪ 60 ቀናት የበጀት ዓመቱን ገቢ ዕቅድ መቶ በመቶ መጨረስ እና የ2019 ግብ ማስቀመጥ እንደሚገባ ቢሮ ሃላፊው በተቀመጠው የጊዜ ሰሌዳ እንዲያስፈፅሙ አሳስበዋል።
1. የደረጃ “ለ” የቀን ገቢ ጥናት በአዲሱ የገቢ ግብር አዋጅ 130/2018 መሠረት በጥንቃቄ መመራት ማስፈፀም (ጊዜው የሚወሰን)፣
2. ኪራይ ገቢ ያልከፈሉትን ግብር ከፋዮች ተከታትሎ ማስከፈል እስከ ግንቦት 10/2018 ዓ.ም፣
3. የሩብ ዓመት 25% ቅድመ-ግብር ያልከፈሉትን ግብር ከፋዮች እስከ ግንቦት 10/2018 ዓ.ም፣ ተከታትሎ ማስከፈል፣
4. አማራጭ አነስተኛ ግብር 2.5 ያልከፈሉትን ግብር ከፋዮች እስከ ሚያዝያ 10/2018 ዓ.ም፣ ተከታትሎ ማስከፈል፣
5. የደረጃ “ሀ” እና ደረጃ “ለ” ዳግም ውሳኔ ወስኖ ማስከፈል እስከ ግንቦት 10/2018 ዓ.ም፣
6. ወርሃዊ የተጨማሪ እሴት ታክስ ሪፖርት ማስደረግና ማስፈፀም እስከ ሰኔ 30/2018 ዓ.ም፣
7. የተጨማሪ እሴት ታክስ በልዩነት ወስኖ ማስከፈል እስከ ሰኔ 30/2018 ዓ.ም፣
8. ሌሎች ያልተጠቀሱ የመደበኛ ገቢዎች ላይ ርብርብ ማድረግና ገቢውን መሰብሰብ በዚህ ስር ያልተጠቀሱ መደበኛ ገቢ ላይ ሮያሊቲ ገቢን ከምንጩ ተከታትሎ መሰብሰብና ዕቅድን መቶ በመቶ መሰብሰብ እስከ ሰኔ 30/2018 ዓ.ም፣
የእርሻ ስራ ግብር እና የገጠር መጠቀምያን በተለያዩ ስልቶች በመጠቀም መጨረስ እስከ ግንቦት 15/2018 ዓ.ም፣
ተርን ኦቨር ታክስ ሰብስበው ገንዘቡን ለገቢ ተቋሙ ያላስገቡ ካሉ ተከታትሎ የማስገባት ስራ መጠናቀቅ አለበት (ቀኑ ይወሰናል) ።
ውዝፍና መደበኛ ግብር ተከታትሎ ማስከፈል እስከ ግንቦት 10/2018 ዓ.ም፣
የ2018 በጀት ዓመት ተግባራትን ለሚቀጥለው በጀት ዓመት ሳያሻገሩ በአዲስ መንፈስ እና ብሩህ ተስፋ ለአዲሱ በጀት ዓመት በዝግጅት ምዕራፍ ማጠናቀቅ እንዳለበት ቢሮ ሃላፊው ጥብቅ መመሪያ ሰጥተዋል።።
ከደንበኞች አገልግሎት አኳያ ነባር የግብር ከፋይ መለያ ቁጥር ያላቸውን ከዲጅታል መታወቂያ ጋር በማስተሳሰር እሰከ ሰኔ 30/2018 ማጠናቀቅ ይገባል ብለዋል።
የገቢዎች መምሪያ፣ ጽህፈት ቤት ሃላፊዎች እንዲሁም የስራ ሂደት ዳይሬክተሮች፤ መንግስት ያስቀመጠውን ግብር ሰብስቦ የክልሉን ልማት የማገዝ ተልዕኮ ለመወጣት ስራወችን በቁርጠኝነት እንዲያስፈፅሙ የአደራ መልክዕት አስቀምጠዋል።
ሁላችንም አመራርና ፈጻሚዎች “እንዳንድ ቃል ተናጋሪ እንዳንድ ልብ መካሪ” ሁነን ችግር ሲገጥመን እየተመካከርን የህዝባችንን የልማት ተጠቃሚነት ለማድረጋገጥ በጋራ እንስራ የሚል መልዕክት አስተላልፈዋል።
በደሴ ገላው