20/04/2026
የአማራ ገጠር መንገዶች ኮንስትራክሽን ኤጀንሲ ባለፉት 9 ወራት 48.34 ኪ.ሜ የመንገድ ግንባታ እና ከ4 ሽህ ኪ.ሜ በላይ በላይ የነባር መንገዶች ጥገና ማከናወኑ ተገለፀ፡፡
የአማራ ገጠር መንገዶች ኮንስትራክሽን ኤጀንሲ የ2018 ዓ.ም የ9 ወራት ዕቅድ አፈፃፀም ግምገማ በ12/08/2018 ዓ.ም በተካሄደበት ወቅት እንደተገለፀዉ ኤጀንሲዉ ባለፉት 9 ወራት 56.08 ኪ.ሜ የመንገድ ግንባታ ለማከናወን አቅዶ 48.34 ኪ.ሜ መንገድ በመገንባት የ9 ወሩን ዕቅድ 86.2%፣የዓመቱን ዕቅድ ደግሞ 47.32% ፈፅሟል፡፡ የተለያየ መጠን ባላቸዉ ስትራክቸሮች ግንባታ በበጀት ዓመቱ 227 የተለያየ መጠን ያላዉ ስትራክቸሮች ለመገንባት ታቅዶ በ153 የተለያየ መጠን ባላቸዉ ስትራክቸሮች በተለያየ የአፈፃፀም ደረጃ ላይ የሚገኙ ግንባታዎች እየተከናወኑ እንደሆነ በዉይይቱ ተገልፆል፡፡
በነባር ገጠር መንገዶች ጥገና ዘርፍ ኤጀንሲዉ ባለፉት 9ወራት በመደበኛ እና በወቅታዊ የጥገና ዓይነቶች 5,164.61 ኪ.ሜ የነባር ገጠር መንገዶች ጥገና ለማከናወን አቅዶ 4,506.84 ኪ.ሜ መንገድ በመጠገን የ9 ወሩን ዕቅድ 87.26%፣የዓመቱን ዕቅድ ደግሞ 74.64% ማሳካት እንደተቻለ በዉይይቱ ተመልክቷል፡፡
ኤጀንሲዉ በበጀት ዓመቱ ግንባታ ለማከናወን በዕቅድ ከያዛቸዉ 34 የመንገድ/ድልድይ ፐሮጀክቶች መካከል በፈተና ዉስጥ ሆኖ በ32 ፕሮጀክቶች ግንባታ እያከናወነ እንደሆነ እና የ9 ወሩ አፈፃፀም በበጀት ዓመቱ ከተያዘዉ ዕቅድ አንፃር ሲታይ ዉሱንት ያለበት ቢሆንም ከባለፈዉ ዓመት ተመሣሣይ ወቅት አንፃር ሲታይ ግን የተሻለ እንደሆነ በዉይይቱ ተመልክቷል፡፡
አሁን ላይ በተለይ በዓለም አቀፍ እና ሀገር አቀፍ ደረጃ የተከሰተዉ የነዳጅ እጥረት በግንባታ እና ጥገና ሥራዉ ላይ ጫና እያሳደረ ቢሆንም የሚያጋጥሙ ችግሮችን ተጋፍጦ የግንባታ እና ጥገና ሥራዎችን በማከናወን የኤጀንሲዉን አፈፃፀም ከፍ ለማድረግ ሁሉም የኤጀንሲዉ አመራር እና ሰራተኛ ርብርብ ማድረግ እንዳለበት በዉይይቱ ተገልፆል፡፡አሁን ካለዉ የነዳጅ እጥረት አንፃር ነዳጅን በቁጠባ ለመጠቀም እንዲቻል የስትራክቸር ግንባታዎችን የማከናወን እና በበጀት ዓመቱ ለማጠናቀቅ በዕቅድ ለተያዙ ፕሮጀክቶች ቅድሚያ ትኩረት ሰጥቶ ነዳጅ እና ሌሎቸ የግንባታ ግብዓቶችን ማሟላት እንደሚገባም በዉይይቱ ተመልክቷል፡፡ኤጀንሲዉ በበጀት ዓመቱ 6/ስድስት/ ፕሮጀክቶችን ለማጠናቀቅ አቅዶ እየሰራ እንደሆነ ለዉይይት ከቀረበዉ ሪፖርት ለመረዳት ተችሏል፡፡
በኤጄንሲዉ ዕቅድ አፈፃፀም ዉይይት የኤጀንሲዉ ዋና መ/ቤት አመራሮች እና ሰራተኞች እንዲሁም ከክልሉ ፕላን ኮሚሽን ጥሪ የተደረገላቸዉ ባለሙያዎች ተሣታፊ ሆነዋል፡፡