30/08/2026
የቅጥር ማስታወቂያ
የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ በ2019 በጀት ዓመት የተቋሙን የሰው ኃይል ለማጠናከር በሁሉም ክልሎችና በሁለቱ ከተማ አስተዳደር ውስጥ የሚገኙ ብሔር ብሔረሰብና ሕዝቦች፣ የጾታ ተዋፅዖን ከግምት ውስጥ ባስገባ መልኩ ተመልምለው በተቋሙ ባሉት ልዩ ልዩ የሥራ ዘርፎች ተመድበው ማገልገል የሚፈልጉ ዕጩ ፖሊሶችን አወዳድሮ ለመቅጠር ይፈልጋል።
ዕጩ ተመልማዮቹ ምልመላው ተጠናቆ ወደ ኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ሥልጠና ማዕከል ገብተው ሥልጠና ከመጀመራቸው በፊት የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ማቋቋሚያ አዋጅ ቁጥር 720/2004 እና ደንብ ቁጥር 268/2005 በሚያዘው መሠረት የ7 ዓመት የሥራ ውል ግዴታ በመግባት በማሰልጠኛ ትምህርት ቤቱ አማካይነት የሚሰጣቸውን ሥልጠና በሚገባ በመከታተል ማጠናቀቅ ይጠበቅባቸዋል፡፡
በሥልጠና ቆይታ ጊዜያቶችም በማሠልጠኛ ትምህርት ቤቱ በኩል የምግብ፣ የመኝታ፣ የሕክምና እና ለሥልጠናው የሚያስፈልጉ የአልባሳት፣ የትምህርት መርጃ መሳሪያዎችና የኪስ ገንዘብ ይሰጣል።
ሥልጠናው ሲጠናቀቅም እያንዳንዱ ተመራቂ በተቋሙ የደመወዝ ስኬል መሰረት ወርሃዊ ደመወዝና የቀለብ ሂሳብ የሚከፈለው ሆኖ በተቋሙ ልዩ ልዩ የስራ አልባሳት፣ ነፃ የሕክምና አገልግሎት፣ በካምፕ የጋራ መኖሪያ ቤት እንዲሁም የትራንስፖርት አገልግሎት ያገኛሉ።
ተመርቀው ፖሊሳዊ የሙያ አገልግሎት በሚያበረክቱባቸው ጊዜያትም በተቋሙ ውስጥ በኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ማቋቋሚያ አዋጅ፣ ደንብ እና የስልጠና መመሪያዎች መሠረት በሚወጡ መመዘኛዎች አማካኝነት በልዩ ልዩ የትምህርትና ሥልጠና ፕሮግራሞች በመወዳደር ተጠቃሚ የመሆን ሠፊ ዕድል የሚጠብቃቸው መሆኑን የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ በደስታ ይገለፃል።
የምልመላ መስፈርት (መመዘኛ)
1. ዜግነት ኢትዮጵያዊ የሆነ/የሆነች፣
2. ለሕገ-መንግስንቱና ለሀገሪቱ ሕጎች ተገዥና ታማኝ የሆነ/የሆነች፣
3. ከማናቸውም ደባል ሱሶች የፀዳ/የፀዳች እና መልካም ስነ-ምግባር ያለው/ያላት፣
4. በሚመለመልበት አካባቢ ነዋሪ ስለመሆኑ የቀበሌ መታወቂያ ወይም የፋይዳ መታወቂያ ማቅረብ የሚችል/የምትችል፣
5. ከሚኖርበት ቀበሌ አስተዳደር፣ ከአካባቢው ፖሊስ እና ከተማረበት ትምህርት ቤት የተዘጋጁ ቅፆችን በማስሞላት ማስረጃ ማቅረብ የሚችል/የምትችል፤
6. በብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች እንዲሁም በሃይማኖት እኩልነት የሚያምን/የምታምን፣
7. ለፖሊስነት የሚያበቃ ሙሉ ጤናማ መሆኑን/መሆኗን በህክምና የተረጋገጠ ማስረጃ ማቅረብ የሚችል/የምትችል፣
8. ዕድሜው/ዋ ከ18 እስከ 25 ዓመት ያላነሰና ያልበለጠ/ያልበለጠች፣
9. የማንኛውም የፖለቲካ ድርጅት አባል ያልሆነ/ያልሆነች፣
10. የትምህርት ደረጃ 10ኛ ክፍል እና በላይ የሆነ/የሆነች እንዲሁም ትምህርት ያጠናቀቀበት ካርድ ዋናውንና የማይመለስ አንድ ፎቶ ኮፒ ማቅረብ የሚችል/የምትችል፣
11. ብዝሃነትንና አካታችነትን ለማረጋገጥ ሲባል ያልተካተቱና አነስተኛ ቁጥር ባለባቸው ብሔሮች አካባቢ ለሚመለመሉ ወጣቶች ቢያንስ 6ኛ ክፍል እና በላይ የሆነ/የሆነች፣
12. ቁመት ለወንድ 1.65 ሜትር በላይ የሆነ፣ ለሴት 1.60 ሜትር በላይ የሆነች፣
13. የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ኮሚሽን ማቋቋሚያ አዋጅ ቁጥር 720/2004 እና ደንብ ቁጥር 268/2005 በተደነገገው መሠረት የ7 ዓመት የሥራ ውል ግዴታ በመግባት ሥልጠናው ሲጠናቀቅ በየትኛውም የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ ተቋም የሥራ አከባቢ ተመድቦ/ተመድባ ለመሥራት ፈቃደኛ የሆነ/የሆነች፣
14. ከአሁን በፊት በወንጀል ተከሶ ያልተቀጣ/ያልተቀጣች ወይም የወንጀል ሪከርድ የሌለበት/የሌለባት የአሻራ ምርመራ ለማድረግ ፍቃደኛ የሆነ/የሆነች፣
15. ከአሁን በፊት በማንኛውም የፖሊስ እና የመከላከያ ሰራዊት ተቋም ሥልጠና ያልተሳተፈ/ያልተሳተፈች ወይም በአባልነት ተቀጥሮ ያልሰራ/ያልሰራች፤
16. ያላገባ እና ያልወለደ ወይም ያላገባች እና ያልወለደች፣
ማሳሰቢያ፡- ማንኛውም ዕጩ ተመልማይ በምዝገባ ወቅት ከላይ የተገለፁት መመዘኛዎች እንደተጠበቁ ሆኖ ከዚህ በታች የተዘረዘሩትን ማስረጃዎች ይዞ በመቅረብ መመዝገብ ይኖርበታል፡፡
1) የትምህርት ማስረጃ ዋናውንና የማይመለስ 1 ፎቶ ኮፒ፣
2) ከ2 ዓመት በላይ ነዋሪነትን የሚያመለክት የቀበሌ ነዋሪነት መታወቂያ ወይም የፋይዳ መታወቂያ ይዞ መቅረብና መመዝገብ ይጠበቅበታል፣
3) የተመልማዩን ማንነት አጠቃላይ ሁኔታ ለመገንዘብ እንዲያስችል ታስቦ በሥልጠና ማዕከሉ አማካይነት የተዘጋጀውን ፎርም ከምዝገባ ጣቢያውን በመቀበል የመጨረሻ አመት ካጠናቀቀበት ወይም ካጠናቀቀችበት ትምህርት ቤት፣ ከመኖሪያ ቀበሌና ከአከባቢው የማህበረሰብ አቀፍ ፖሊስ ጽ/ቤት ቀርቦ ወይም ቀርባ የማስሞላትና በተጠቀሰው የቀን ገደብ መሰረት ለምልመላ ጣቢያው አስቀድሞ ማስረከብ ይጠበቅባቸዋል፡፡
4) ሴት ተወዳዳሪዎች ይበረታታሉ።
ማንኛውም ምልምል ከ500 ብር በላይ፣ ወርቅ፣ የተለያዩ ስለታማ ነገሮችን፣ ምግብ ነክ ነገሮች እና ከሁለት ቅያሪ ልብስ በላይ ይዞ ወደ ማሰልጠኛው ማዕከል መግባት የተከለከለ ነው፡፡
የምዝገባ ጊዜው ከጳጉሜን 3 ቀን 2018 ዓ.ም እስከ መስከረም 18 ቀን 2019 ዓ.ም ባሉት ተከታታይ የሥራ ቀናት የሚካሄድ ሲሆን፣ መስፈርቱን የምታሟሉ አመልካቾች በየክልሉ በሚገኙ ዞኖች፣ ወረዳዎች እና በምልመላ ጣቢያዎች በአካል በመቅረብ መመዝገብ የምትችሉ መሆኑን እንገልጻለን።