01/06/2026
ድምጽ የመስጠት ሒደቱ እስከ ዕኩለ ሌሊት 6 ሰዓት ድረስ ተራዘመ
አዲስ አበባ፣ ግንቦት 24፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) የ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ድምጽ የመስጠት ሒደት እስከ ዕኩለ ሌሊት 6 ሰዓት ድረስ ተራዝሟል አለ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ፡፡
ምርጫ ቦርድ ጉዳዩን አስመልክቶ ባወጣው መግለጫ÷ ዛሬ ሰኞ ግንቦት 24 ቀን 2018 ዓ.ም ከማለዳ 12 ሰዓት ጀምሮ እስከ ምሽት 12 ሰዓት የ7ኛውን ጠቅላላ ምርጫ ድምፅ የማስፈጸም ሒደት ላይ እንደነበር ጠቅሷል፡፡
ቦርዱ በሥምሪት ላይ ያለው የክትትል ቡድኑ ያቀረበለትን ሪፖርት ተመልክቶ ውሳኔ ማሳለፉን አመልክቷል፡፡
በኢትዮጵያ የምርጫ፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባና የምርጫ ሥነ ምግባር ዐዋጅ 1162/2011 አንቀጽ 49(4) መሠረት ቦርዱ የምርጫው ነፃና ፍትሐዊነት ይበልጥ ያሰፍናል ብሎ ካመነ የድምፅ መስጫ ሰዓቱን ሊያራዝም እንደሚችል በግልጽ ይደነግጋል።
በዚህ መሰረትም የድምጽ መስጫ ሒደት ባልተጠናቀቀባቸው የምርጫ ጣቢያዎች ላይ ድምጽ የመስጠት ሒደቱ እስከ ዕኩለ ሌሊት 6 ሰዓት ድረስ የተራዘመ መሆኑን ነው ቦርዱ ያስታወቀው፡፡
የተመዘገቡ መራጮች መርጠው የተጠናቀቁባቸው ጣቢያዎች ላይ አስፈጻሚዎች የድምፅ ቆጠራ ሒደቱን እንዲያከናውኑም ቦርዱ አሳስቧል፡፡
#ኢትዮጵያ #ኢትዮጵያእየመረጠችነው #በምርጫብቻ #ፋናዲጂታል