29/08/2026
በክረምት ወራት ሲያስተምራቸው የቆዬ ተማሪዎችን አስመረቀ ።
**************************
ደጀንከተማ ኮምዬኒኬሽን ነሀሴ 23/2018 ዓ/ም
ላይፍ ላይን አካዳሚ በክረምት ወራት በተለያዬ የትምህርት ዘርፎች ሲያስተምራቸው የቆዬ ተማሪዎችን በዛሬው እለት አስመርቋል ።
የፕሮግራሙን የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የደጀን ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ጽ/ቤት ሀላፊ አቶ ፍቅረሰብ አለሙ ሲሆኑ የዚችን ሀገር ተረካቢ ህፃናትን የሚገባቸውን እንክብካቤና ፍቅር ከመስጠት ባሻገር በእውቀትና በስነ ምግባር ኮትኩቶ የማሳደግ ሀላፎነትም ያስፈልጋል ይህ ደግሞ እሚጀምረው ከህፃናት ነው አንድን ዛፍ መጣመም ሲጀምር ከቡቃያው ጀምረን ካላቃናነው እና ካላስተካከልነው ካደገ በኋላ ለማስተካከል ብንሞክር እንደማይቻል ሁሉ ህፃናትንም በዚህ እድሚያቸው ትክክለኛውን መንገድ እያሳየንና በስነ ምግባር እየኮተኮትን ግብረ ገብነትን እያሳየን ካላሳደግናቸው ካደጉ በኋላ ለማስተካከል ይከብደናል ከዚህ ረገድ ላይፍ ላይን አካዳሚ እያደረገ ያለው ትውልድን የመቅረፅ ሂደት የሚያስመሰግን በመሆኑ በዚሁ አጋጣሚ አክብሮቴን ለመግለጽ እወዳለሁ ያሉት ሀላፊው ይህን መልካም ተግባራችሁንም ወደ ፊት አጠናክራቸሁ እንደምትቀጥሉ አልጠራጠርም በማለት ተናግረዋል ።
ይህን ት/ቤት እዚህ ለማድረስ ብዙ ውጣ ውረዶች እንዳሳለፍና አሁንም ብዙ ችግሮች ቢኖሩም ትውልድን በማነጽ ረገድ ተግባሮችን ለማስቀጥል ወደ ኋላ እንደማይሉ የተናገሩት የት/ቤቱ መስራችና ር/መምህር አቶ ደሳለኝ ሙሉጌታ ሲሆኑ በክረምት ወራት ህፃናት ጊዜያቸው በከንቱ እንዳያሳልፍና ለቀጣይ መደበኛ ትምህርት ማጠናከሪያ እንዲሆናቸው በተጨማሪም የቋንቋ ንግግር ክህሎታቸውን ለማዳበር እና ከዛም በላይ የስነ ምግባርና የግብረ ገብ ትምህርቶች የሀይማኖት እኩልነትን ባሰፈነ መልኩ ሀይማኖታዊ ትምህርቶችን ልምድ ባላቸው መምህራን ሲሰጡ መቆየታቸውን ገልፀዋል ። አቶ ደሳለኝ አያይዘውም በ2019 ዓ/ም የትምህርት ዓመት በአዲስ ት/ቤት በአዲስ መልኩ ምዝገባ የጀመርን በመሆኑ ወላጆች አዲሱ ት/ቤታችን መብራት ሀይል ይሰራበት የነበረ ግቢ ውስጥ ስለሆነ ያለን ክፍት ቦታ አነስተኛ በመሆኑ ልጆቻችሁን እየመጣችሁ እንድታስመዘግቡ በማለት ጥሪያቸውን አስተላልፈው ተመራቂ ተማሪዎችንም የእንኳን ደስ አላችሁ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል ።
በእለቱም በተመራቂ ተማሪዎች የተለያዬ የብሄር ብሄረሰብ ውዝዋዜዎች የአብነትና ቁርዓን ትምህርቶች እንዲሁም የእንግሊዘኛ ክህሎትን የሚያዳብሩ ንግግሮች ቀርበዋል።
በመጨረሻም ካርድና የተሻለ ተሳትፎ ለነበራቸው ተማሪዎች የማበረታቻ ሽልማትና ሰርተፍኬት በመስጠት ፕሮግራሙ ተጠናቋል ።