24/08/2026
በቃሉ ወረዳ የገርባ ጤና ጣቢያ የአገልግሎት ጥራትን ለማሻሻል፣ መሰረተ ልማቶችን ለማሟላት እና ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ለማድረግ የሰራቸውን አበራች ስራዎች የሚያመላክት የመስክ ምልከታ ተካሄደ።
ነሀሴ 18/2018 ዓ/ም (ቃሉ ኮሙኒኬሽን)
በዚሁ መድረክ የደቡብ ወሎ ዞን ጤና መምሪያ ም/ሀላፊ አቶ አብዱ መሀመድ፣ የቃሉ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ ሙህዲን አህመድ፣ የወረዳው ምክር ቤት ዋና አፈጉባኤና የጤና ጣቢያው ቦርድ ሰብሳቢ አቶ አረጋ ታደሰ፣ የጤና ጽ/ቤት ሀላፊ አቶ ዳንኤል ጋሻው፣ የጤና አመራሮችና ባለሙያዎች፣ የቀበሌ አሴተዳዳሪዎች፣ የሀገር ሽማግሌዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።
የገርባ ጤና ጣቢያ ሀላፊ አቶ ጀማል አህመድ የጤና ጣቢያውን ንጽህና፣ የጎርፍና የመንገድ ችግሮች በማህበረሰብ ተሳትፎ መፍትሔ ማግኘታቸውን፣ ተጨማሪ ክፍሎችን በመገንባት፣ የCBC ማሽን ስራ ላይ በማዋል እና ከትውልደ-ኢትዮጵያዊያን ባለሀብቶች እስከ 250,000 ብር የሚደርስ የገንዘብና የጄኔሬተር ድጋፍ ቃል ማስገባት መቻሉን ተናግረዋል። በተጨማሪም የ022 እና 023 ጤና ኬላዎች መታደሳቸውን፣ የደንበኞች ምክር ቤት መቋቋሙንና ለተማሪዎች ነፃ የህክምና እና የንጽህና ቁሳቁስ ድጋፍ እየተደረገ መሆኑን ጨምረው በገርባ ጤና ጣቢያና በ023 ጀርጀሮ ቀበሌ ስራ የጀመረውን የኮንምፕረንሲቭ ጤና ኬላ አገልግሎትና የተጀመረውን ግንባታ አስመልክተው ገለፃ አዶርገዋል።
በመድረኩም የወረዳው ምክር ቤት ዋና አፈጉባኤና የጤና ጣቢያው የቦርድ ሰብሳቢ አቶ አረጋ ታደሰ የጤና ጣቢያው ባለሙያዎች በተለየ ተነሳሽነት በመስራታቸው ተቋሙን ማራኪ ገፅታን በማላበስ ጥራት ያለው አገልግሎት መስጠት መቻሉን እና የእናቶችና ህፃናት ክፍል ከፍተኛ መሻሻል ማሳየቱን ገልጸዋል። በጤና ተቋሙጰግቢውን በማስፋፋትና የቀዶ ሕክምና ክፍል (OR) ከተገነባ የሕክምና ቁሳቁሶችን ሙሉ በሙሉ ለማሟላት ቃል የገባ ባለሀብት በመኖሩ የህብረተሰቡ ርብርብ እንደሚያስፈልግም ጠቁመዋል።
የቃሉ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ሙህዲን አህመድ እንደገለፁት ከአንድ ዓመት በፊት የነበረውን የቅሬታ ምንጭ በመቀየር፣ በተደረገ ጤናማ ፉክክር የጤና ጣቢያው የውስጥና የውጭ ገጽታ፣ ጽዳትና ማራኪነት በከፍተኛ ደረጃ መሻሻሉን ተናግረዋል። በሆስፒታል ደረጃ የሚገኙ መሳሪያዎች እንደ CBC እና አልትራሳውንድ በማህበረሰብና በድጋፍ የተሟሉ ሲሆን፣ የመድኃኒት አቅርቦት 99% ማድረስ ተችሏል። ከ56 የላቦራቶሪ መመርመሪያ ዓይነቶች 48ቱ አገልግሎት እየሰጡ ይገኛሉ ብለዋል።
የጤና ጣቢያው ዋናው ፈተና የቦታ ማስፋፊያ መሆኑን የጠቆሙት አቶ ሙህዲን፣ ግቢውን የማስፋት ስራ ከተሰራ ለግንባታው ወረዳው በጀት በመመደብ ግንባታ ማካሄድ እንደሚችልና ግብአቶችንም ለማሟላት አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል። ለተሰራው ስኬታማ ስራ ሚና ለነበራቸው አካላት ሁሉ ምስጋናቸውን አቅርበዋል።
የደቡብ ወሎ ዞን ጤና መምሪያ ም/ሀላፊ አቶ አብዱ መሃመድ በበኩላቸው ቃሉ ወረዳ በዞኑ ካሉ ወረዳዎች ጋር ተወዳድሮ በክልሉ ጤና ቢሮ አንደኛ በመውጣት ያስመዘገበው ውጤት የሚደነቅ ሲሆን፣ የጤና ተቋማትን ቀረብ ብሎ በመምራትና በጤናማ ውድድር የተገኘው ተሞክሮ ወደ ሙሉ ዞኑ ሊሰፋ እንደሚገባ ገልጸዋል።
በተከለሰው የጤና ኤክስቴንሽን ፖሊሲ መሰረት ባለፈው ዓመት 34 አጠቃላይ ጤና ኬላዎች ደረጃቸው የተሻሻለ ሲሆን፣ በ2019 ዓ.ም ደግሞ 40 አዳዲስ አጠቃላይ ጤና ኬላዎችን በ20 ወረዳዎች ለማስፋፋት መታቀዱን ጠቁመዋል። የላቦራቶሪ፣ የክትባትና የወሊድ ክፍሎች መዘመናቸውንና የመድኃኒት አቅርቦት እስከ 100% መሸፈኑን አበክረው የገለፁት አቶ አብዱ፤ የዞኑ ጤና መምሪያና የክልሉ ጤና ቢሮ በግብአት፣ በስልጠናና በቴክኖሎጂ ድጋፋቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል። አሁን ያለው የገርባ ጤና ጣቢያ ቦታ ጠባብ በመሆኑም ህብረተሰቡና አመራሩ ተባብረው ግቢውን በአስቸኳይ እንዲያስፋፉ አደራ ብለዋል።
በመጨረሻም ለውጤቱ መመዝገብ ወሳኝ ሚና ለነበራቸው የተለያዩ የጤና ባለድርሻ አካላትና ተቋማት የእውቅናና ምስጋና መርሃግብር ተካሂዷል።