23/08/2026
በመሬት ዘርፍ የማዘጋጃ ቤታዊ ገቢን ለማሳደግ የአቅም ግንባታ ስልጠና ተሰጠ።
በድሬዳዋ አስተዳደር ከመሬት ዘርፍ የሚመነጨውን የማዘጋጃ ቤታዊ ገቢ በተሻለ ሁኔታ ለማሰባሰብና የገቢ አፈጻጸምን ለማሳደግ ያለመ የአቅም ግንባታ ስልጠና ተሰጠ።
ስልጠናው በመሬት ዘርፍ የሚመነጩ የገቢ ምንጮችን በአግባቡ መለየት፣ የገቢ አሰባሰብ ሂደትን ማጠናከር፣ የገቢ ግብ አፈጻጸምን በተገቢው መከታተል እና በመሬት አስተዳደር ሥራና በማዘጋጃ ቤታዊ ገቢ መካከል ያለውን ትስስር ማጠናከር ላይ ትኩረት አድርጓል።
በመድረኩ በተለይም በቦታ ደረጃ የሊዝ መነሻ ዋጋና በስም ዝውውር ወቅት የሚያገለግለውን ወቅታዊ የተመን ዋጋ አሰራር በተመለከተ ለአመራርና ለሠራተኞች ሰፊ ገለጻ ተሰጥቷል።
የመሬት ባንክና ማስተላለፍ ዳይሬክተር አቶ ረመዳን ሙሳ የመሬት ገቢን ለማሳደግ የአሰራር ማሻሻያዎችን መተግበር፣ የመሬት ልማትና አጠቃቀምን በተቀናጀ ሁኔታ መምራት እና የመሬት ሀብትን በውጤታማነት በመጠቀም ከመሬት የሚገኘውን ገቢ በሙሉ አቅም ማሰባሰብ እንደሚገባ አቅጣጫ ሰጥተዋል።
በተያዘው በጀት አመት ቢሮው 1.4 ቢልየን ብር ገቢን ለመሰብሰብ በእቅድ መያዙን የገለጹት ዳይሬክተሩ ለዚህም ስኬት መትጋት ይገባል ብለዋል።
በተጨማሪም የመሬት ገቢ አፈጻጸምን በቁጥርና በውጤት መለካት፣ የገቢ ክፍተቶችን በመለየት የማስተካከያ እርምጃ መውሰድ፣ የገቢ ምንጮችን ማስፋት እንዲሁም በሥራው ላይ ግልጽነት፣ ተጠያቂነትና ቅንጅትን ማጠናከር እንደሚገባ ተጠቁሟል።
የተቋም ለውጥ አፈጻጸምና አገልግሎት ስታንዳርዳይዜሽን ምዘና ዳይሬክተር አቶ ኢብሳ አሜ፣ ስልጠናው የመሬት ዘርፍ ገቢን ከከተማዋ የልማት ፍላጎት ጋር በማጣጣም፣ የመሬት ሀብትን በአግባቡ በማስተዳደር ዘላቂ ገቢ ለማመንጨት የሚያስችል አቅም ለመገንባት ያለመ መሆኑን ገልጸዋል።
ተሳታፊዎችም በመሬት ዘርፍ የገቢ አሰባሰብና አስተዳደር ላይ የሚታዩ ችግሮችን በመለየት በስራ ላይ እያጋጠሙ የሚገኙ ክፍተቶችን በማንሳት የመፍትሔ አቅጣጫዎች ላይ ተወያይተዋል።
በመጨረሻም የመሬት ዘርፍ ገቢ የማዘጋጃ ቤታዊ ገቢ ዋና አካል በመሆኑ፣ የገቢ አሰባሰብ ሥራን በተቀናጀ፣ በግልጽነትና በውጤታማነት ማከናወን የከተማዋን የልማት አቅም ለማጠናከር ወሳኝ መሆኑ ተጠቁሟል።
ነሃሴ 17 ቀን 2018 ዓ.ም