30/05/2026
የድሬዳዋ አስተዳደር ጤና ቢሮ ከ JSI ኢትዮጵያ ጋር በመተባበር በ2018 ዓ.ም በተመረጡ ጤና ተቋማት የተጀመሩ የጥራት ማሻሻያ ፕሮጀክቶች (Quality Improvement Projects) ያሉበትን የአፈፃፀም ግምገማና የልምድ ልውውጥ መድረክ አካሂዷል።
መድረኩ በጤና ተቋማት የመረጃ ጥራት፣ የሪፖርት ተመጣጣኝነት፣ የአገልግሎት ክትትልና የውሳኔ አሰጣጥ ሂደቶችን ለማሻሻል እየተከናወኑ ያሉ ስራዎችን በጋራ ለመገምገምና ቀጣይ የስራ አቅጣጫዎችን ለማስቀመጥ ያለመ መሆኑን ተገልጿል።
በአስተዳደሩ ጤና ቢሮ በዕቅድ፣ ክትትልና ግምገማ ዳይሬክቶሬት የጤና መረጃ አስተዳደር ስርዓት አስተባባሪ አቶ ነጋ ጌትነት እንደገለፁት በአስተዳደሩ የሚታዩ የዝቅተኛ አፈፃፀም ጠቋሚዎች(low performing indicators) ለመቀየር የጥራት ማሻሻያ ፕሮጀክቶች ትልቅ ሚና እንዳላቸው በመግለፅ በተለይም በመረጃ ጥራት፣ በሪፖርት ተመጣጣኝነት፣ በመድሐኒት አቅርቦትና በአገልግሎት ክትትል ረገድ የሚታዩ ክፍተቶችን በመለየት በማስረጃ ላይ የተመሰረቱ መፍትሄዎችን መተግበር አስፈላጊ መሆኑን አሳስበዋል።
አቶ ነጋ አክለውም የጤና መረጃ ለትክክለኛ ውሳኔ መሰረት በመሆኑ በጤና ተቋማት የሚመነጩ መረጃዎች ትክክለኛ፣ ወቅታዊና ተመጣጣኝ መሆን እንዳለባቸው ገልፀው፣ በተለይም በጤና ተቋማት ደረጃ የሚታዩ የመረጃ ልዩነቶችና የሪፖርት አለመጣጣሞች በአገልግሎት እቅድ፣ በመድሐኒት ስርጭትና በሀብት አጠቃቀም ላይ አሉታዊ ተፅእኖ እንደሚያሳድሩ አብራርተዋል።
በመድረኩም ሁለት ዋና ዋና የጥራት ማሻሻያ ፕሮጀክቶች የቀረቡ ሲሆን፤ የመጀመሪያው “In-depth Data Quality Analysis (Triangulation) of Family Planning Program Vs Supply Reports” የተሰኘ የጥራት ማሻሻያ ፕሮጀክት ሲሆን ይህም በቤተሰብ ዕቅድ አገልግሎት ተጠቃሚዎች ቁጥር እና በመድሐኒት አቅርቦት ሪፖርቶች መካከል ያለውን የመረጃ ልዩነት በመተንተን ተመጣጣኝና ታማኝ መረጃ እንዲኖር ለማስቻል የተዘጋጀ መሆኑ በድሬዳዋ አስተዳደር ጤና ቢሮ የእናቶች ጤና አገልግሎትና ቤተሰብ ዕቅድ ባለሙያ የሆኑት አቶ ደጉ ኩኖ ገልፀዋል።
ፕሮጀክቱ ለተጠቃሚዎች ወቅታዊና ቀጣይ የቤተሰብ ዕቅድ የመድሐኒት አቅርቦት እንዲኖር እንዲሁም በጤና ተቋማት የሚከሰተውን የመድሐኒት ብክነትና የአገልግሎት መሰጫ መሳሪያ እጥረት ለመቀነስ እንደሚያግዝና በተለይም ትክክለኛ መረጃ መኖሩ ለትክክለኛ የመድሐኒት ትንበያና አቅርቦት ውሳኔ ለመስጠት እንደሚያስችልም ተጠቅሷል።
ሁለተኛው “Scaling-up Report Consistency of Under Five Children Diarrhea Disease versus service report” የተሰኘ የጥራት ማሻሻያ ፕሮጀክት ሲሆን፣ በሪፖርቶች ላይ የሚታዩ የመረጃ አለመጣጣሞችን ለመቀነስ ያለመና ፕሮጀክቱ መጀመሪያ በተመረጡ ጤና ተቋማት በሙከራ ደረጃ ተተግብሮ በአፈፃፀሙም የሪፖርት ተመጣጣኝነትና የመረጃ ጥራት ላይ አበረታች ለውጥ መታየቱ ተገልጿል።
የጤና ተቋማት የጥራት አስተባባሪዎችና ባለሞያዎች፣ የጤና መረጃ ባለሙያዎች፣ የፕሮግራም አስተባባሪዎች፣ እንዲሁም የሚመለከታቸው አጋር አካላት በመድረኩ ተሳትፈዋል።
የድሬዳዋ አስተዳደር ጤና ቢሮ ኮሙዩኒኬሽን
22/09/2018 ዓ.ም