05/09/2026
የጋምቤላ ክልል ሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ ለአቅመ ደካማ ወገኖች የሚያደርገውን የበጎ ፈቃድ አገልግሎት በማጠናከር በጋምቤላ ከተማ 04 ቀበሌ ለምትገኝ አንዲት አቅመ ደካማ እናት ቤት የመሥራት ሥራ ጀመረ።
ቢሮው በበጎ ፈቃድ አገልግሎት የተቸገሩ ወገኖችን ለመደገፍ ያቀደው መርሃ ግብር፣ በከተማው በሚገኙ አምስቱም ቀበሌዎች በየስድስት ወሩ አንድ አንድ ቤት በመሥራት ተጠቃሚዎችን ለመደገፍ ያለመ ነው።
የቤት ግንባታ ፕሮግራሙ የቢሮው ሰራተኞች በበጎ ፈቃድ በሚያደርጉት አስተዋጽኦ የሚከናወን ሲሆን፣ በዚህም በተጨማሪ ለአቅመ ደካማ ወገኖች ተጨባጭ ድጋፍ ከማድረግ ባለፈ የመረዳዳትና የመተባበር ባህልን ለማጠናከር ያግዛል።
በዛሬው ዕለት በ04 ቀበሌ የተጀመረው የቤት ግንባታ ሥራም የዚሁ መርሃ ግብር አካል ሲሆን፣ ቢሮው በቀጣይም በአምስቱም ቀበሌዎች በተያዘው ዕቅድ መሠረት ተግባሩን እንደሚያስፋፋ ተገልጿል።
በመርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት የጋምቤላ ክልል ሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ አሪያት ኡጁሉ፣ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ችግረኛና አቅመ ደካማ ወገኖችን በመደገፍ የማህበረሰቡን የመረዳዳት መንፈስ የሚያጠናክር መሆኑን ገልጸዋል።
ወይዘሮ አሪያት እንዳሉት፣ የቢሮው ሰራተኞች በጋራ በመሆን በየስድስት ወሩ አንድ ቤት ለመሥራት ያቀደው ዕቅድ ተግባራዊ በማድረግ በእውነተኛ የበጎ ፈቃድ ሥራ ለተቸገሩ ወገኖች የሚደርሰውን ድጋፍ ማጠናከር ያስፈልጋል ብለዋል።
የቢሮው የሴቶች ግንዛቤ ንቅናቄ ማስፋፊያ ዳይሬክተር አቶ ግሩም ገ/የሱስ በመርሃ ግብሩ ላይ ባደረጉት ንግግር፣ የበጎ ፈቃድ ሥራ እንደ ተቋም ብቻ ሳይሆን እንደ ማህበረሰብ ሊጎለብት የሚገባ እሴት መሆኑን ጠቁመው፣ ሰራተኞችና ሌሎች የማህበረሰቡ ክፍሎች በዚህ መልካም ተግባር እንዲሳተፉ ጥሪ አቅርበዋል።
ቢሮው ከቤት ግንባታ በተጨማሪ በአዲሱ ዓመት እስከ 500 ለሚደርሱ ተማሪዎች የትምህርት ቁሳቁስ እንዲሁም ለሴቶች የንፅህና መጠበቂያ ቁሳቁሶችን ለማቅረብ አቅዷል።
እንዲሁም ለአዲሱ ዓመት የመዓድ ማጋራት መርሃ ግብር በማካሄድ ከተቸገሩ ወገኖች ጋር በመካፈል የበዓል ደስታን በጋራ ለማጣጣም የተለያዩ የበጎ ፈቃድ ተግባራትን ለመፈጸም መዘጋጀቱ ተገልጿል።
በዚህም ቢሮው የበጎ ፈቃድ አገልግሎቱን በማጠናከር አቅመ ደካማ ወገኖችን መደገፍ፣ የተማሪዎችን የትምህርት ተሳትፎ ማጎልበት እና ሴቶች የንፅህና መጠበቂያ ቁሳቁሶችን በተገቢው ሁኔታ እንዲያገኙ ማገዝ የሚያስችሉ ተግባራትን በተቀናጀ መልኩ እያከናወነ መሆኑ ተመልክቷል።