01/06/2026
የሐረሪ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን 7ኛውን ጠቅላላ ምርጫ በCCTV ካሜራ የተደገፈ የፀጥታ ክትትል ሥርዓት እያስጠበቀ ነው።
7ኛው ጠቅላላ ምርጫ በሐረሪ ክልል በሰላምና በተረጋጋ ሁኔታ እየተካሄደ ሲሆን፣ የሐረሪ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን የምርጫውን ሰላምና ደኅንነት ለማስጠበቅ በCCTV ካሜራዎች እና በዘመናዊ የቴክኖሎጂ ሥርዓቶች የተደገፈ የፀጥታ ክትትል ተግባራዊ አድርጓል።
ኮሚሽኑ በምርጫ ጣቢያዎች፣ በድምፅ ቆጠራ ማዕከላት እና በሌሎች ወሳኝ ቦታዎች የተዘረጉ የፀጥታ አውታሮችን በማስተባበር የምርጫውን ሂደት በቅርበት እየተከታተለ መሆኑን ገልጿል።
በተለይም በCCTV ካሜራዎች የተደገፈው የክትትል ሥርዓት የፀጥታ ሁኔታዎችን በእውነተኛ ጊዜ ለመከታተል እና ለሚከሰቱ የፀጥታ ክስተቶች ተገቢና ፈጣን ምላሽ እንዲሰጥ ያስችላል።
የኮሚሽኑ ስትራቴጂክ አመራሮችም በተቀናጀ የትዕዛዝና ቁጥጥር ማዕከል በመገኘት የምርጫውን የፀጥታ ሁኔታ በቀጥታ እየተከታተሉ ሲሆን፣ በየደረጃው የተሰማሩ የፖሊስ አባላትም በከፍተኛ ዝግጁነት ሕዝቡ የዴሞክራሲያዊ መብቱን በነፃነት እንዲጠቀም አስፈላጊውን የፀጥታ አገልግሎት እየሰጡ ይገኛሉ።
የሐረሪ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን የምርጫው ሂደት በሰላም፣ በሕግ የበላይነት እና በሕዝብ እምነት እንዲጠናቀቅ ከማኅበረሰቡ እና ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በቅርበት በመተባበር መስራቱን ገልጾ፣ ሕዝቡም የሰላም እና የሕግ የበላይነት ጥረቶችን እንዲደግፍ ጥሪ አቅርቧል።
ዘጋቢ፡
ሳጅን ዮሐንስ መካ