06/06/2026
የአሮጌው ዘመን አዙሪት ለትውልዱ አይመጥንም!!
የሰው ልጅ የሥልጣኔ ጫፍ ላይ ለመድረስ የሚያደርገው አድካሚ ጉዞ፣ በሐሳብ ልዕልና፣ በምክንያታዊነት፣ በሰላማዊ መስተጋብር፣ እንዲሁም በምርምርና ቴክኖሎጂ ላይ የተገነባ ነው። ፖለቲካዊ ፍላጎትን በጉልበት ለማስፈጸም መሞከር፣ ከሰለጠነ ውይይት ይልቅ የጠመንጃን ቋንቋ መምረጥ፣ ንጹሐንን በመግደልና ተቋማትን በማኮላሸት ስጋትን ማንገስ የትላንቱ የጨለማ ዘመን እንጂ፣ የዛሬውና የነገው የፖለቲካ ስልት ሊሆን ከቶ አይችልም።
የሕዝብን የጠራ ፍላጎት በጠመንጃ አፈሙዝና በፍርሃት ቆፈን ሥር አድርጎ ለማሸነፍ የሚኬድበት አቋራጭ ጎዳና፣ ለዚህ ዘመን የነቃ እሳቤ የማያብር ያረጀና ያፈጀ ስልት ነው። የዛሬው ትውልድ ይህንን የጥፋት አዙሪት በጽኑ አመክንዮ እና በነቃ ተሳትፎው እያመከነው ይገኛል።
የታሪክ ጠባሳ እና የተማርነው እውነት
ያለፉት ዘመናት የታሪክ ማኅደሮቻችንን አቧራ ስናራግፍ፣ ኢትዮጵያ በጠመንጃ ፖለቲካ እና በኃይል እርምጃ ያተረፈችው መቆሚያ የሌለው የደም አበሳ እና የንብረት ውድመት እንጂ፣ ለኩራት የሚበቃ የሥልጣኔ ትሩፋት አልነበረም።
ፖለቲካዊ ልዩነቶችን በሰለጠነ የጠረጴዛ ዙሪያ ውይይት ከመፍታት ይልቅ፣ በየቋጥኙ ሥር መሽጎና ጦር መዝዞ የራስን እውነት በሌሎች ላይ ለመጫን የተደረጉ አፍራሽ ድርጊቶች ሀገሪቱን ለዘመናት ወደ ኋላ ጎትተዋታል። በዚህ ስሑት መንገድ ብዙ ተዳምተናል፣ እጅግ ውድ የሆነ የሰው ሕይወት ገብረናል፤ ዛሬን ብቻ ሳይሆን ነገንም ክፉኛ ጎድቶታል።
የዓለም ተሞክሮ፡ ከጥፋት ወደ ሐሳብ ልዕልና
ዓለም የደረሰችበትን የፖለቲካ ሥልጣኔ ስንቃኝ፣ ያደጉትና የበለጸጉት ሀገራት የደረሱበት የከፍታ ማማ ምስጢር የጠመንጃን አፈሙዝ ዘግተው ሐሳብን በማንገሳቸው መሆኑን እንረዳለን። እንደ ሶማሊያ፣ ሊቢያ እና የመን ያሉ ሀገራት፣ የፖለቲካ ፍላጎትን በኃይል ለማስገደድ በሞከሩ ጽንፈኛ ኃይሎች ሳቢያ ሀገረ መንግሥታቸው ፈርሶ (Failed State) ሕዝባቸው ለከፋ ስደትና መከራ ተዳርጓል።
ከእነዚህ የዓለም አቀፍ ማኅበረሰብ ተሞክሮዎች የምንማረው አንድ ታላቅ እውነት ቢኖር፤ እውነተኛ የፖለቲካ አሸናፊነት የሚረጋገጠው የሕዝብን ልብ በበሳል ፖለቲካዊ ፕሮግራም እና በአሳማኝ ፖሊሲ በመማረክ እንጂ፣ አፈናን በመጠቀም አለመሆኑን ነው። የዘመኑ የኢትዮጵያ ትውልድ ይህንን የሰለጠነ ፖለቲካዊ ሒደት ጠንቅቆ ይገነዘባል፤ ሀገሩም ከተያያዘችው የሥልጣኔ እና የብልጽግና ጎዳና እንድትሰናከል አይፈቅድም።
ነባራዊው እውነታ እና የመንግሥት ጽኑ ጥረቶች
በአሁኑ የኢትዮጵያ ነባራዊ ሁኔታ፣ መንግሥት የሕዝብን የሥልጣን ባለቤትነት ለማረጋገጥ፣ ጠንካራና ገለልተኛ ተቋማትን ለመገንባት እና የዴሞክራሲ ሥርዓትን ለማጽናት በርካታ ወሳኝ እርምጃዎችን እየወሰደ ይገኛል። ብሔራዊ የምክክር ኮሚሽን በማቋቋም ዘመናትን የተሻገሩ ሀገራዊ የፖለቲካ ስብራቶችን ለመጠገን፣ እንዲሁም በቅርቡ የተካሄደውን 7ኛውን ጠቅላላ ምርጫ በስኬት በማጠናቀቅ የሥልጣን ሽግግር ውሳኔ በድምጽ መስጫ ካርድ እንጂ በጥይት እንዳይሆን ሰፊ ጥረት አድርጓል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ፣ አሁንም የአሮጌው ዘመን እንደራሴ ነን ባዮች የራሳቸውን ፖለቲካዊ ፍላጎት በኃይል ለመጫን ይሞክራሉ። የሕዝብን ሰላማዊ ኑሮ ለማወክ ንጹሐንን ዒላማ ያደረጉ ጥቃቶችን በመፈጸም፣ እንዲሁም የዲጂታል ሚዲያዎችን በመጠቀም የሐሰት ትርክትን (Disinformation) በማሰራጨት ሕዝብን ከሕዝብና ከመንግሥት ለማጋጨት ይጥራሉ። ነገር ግን፣ "ውሸት ያሯሩጣል እንጂ አያደርስም" እንደሚባለው ጥልቅ አባባል፣ የእነዚህ ኃይሎች የሐሰት ፕሮፓጋንዳ እና የተንኮል ሴራ በጊዜ ሒደት ገመናው እየተገለጠ፣ በነቃው ሕዝብ ፊት እርቃኑን እየቀረ ይገኛል። መንግሥት እነዚህን የጥፋት ኃይሎች በሕግ አግባብ ከመመከት ባለፈ፣ ትዕግስትንና ሆደ ሰፊነትን መርሆው በማድረግ ለሰላም የዘረጋው እጅ፣ ለሀገር ግንባታ ያለውን ጽኑ ቁርጠኝነት የሚያሳይ ታላቅ ማሳያ ነው።
ትውልዱ ይህንን ሀገራዊ እውነት ጠንቅቆ ተረድቷል። አሁን ያለንበት የ2018 ዓ.ም የኢትዮጵያ የትንሣኤ ዘመን፣ የቴክኖሎጂ ፈጠራና የመስፈንጠሪያ ዘመን እንጂ፣ ወደ ኋላ ተመልሰን በሽፍትነት የአሮጌውን ዘመን የጥፋት አዙሪት የምንለማመድበት ጊዜ አይደለም። ሀገረ መንግሥቱ ከሕዝቡ ጋር በመቀናጀት የሚያደርገውን የሕግ የበላይነት የማስከበር፣ ሰላምን የማረጋገጥ እና ልማትን የማፋጠን ጉዞ፣ አዲሱ ትውልድ በሙሉ አቅሙ ይደግፈዋል።
የፖለቲካ ፍላጎትን በጠመንጃ እና በሐሰት ትርክት ለማስፈጸም የሚደረገው ጥረት በመቃብር ያለ፣ ያለፈ ዘመን ትርክት ነው። ዛሬ ላይ የሐሳብ ልዕልና፣ የምክንያታዊነት እና የዴሞክራሲያዊ ውይይት ድምጽ ከፍ ብሎ እየተሰማ ነው። ትውልዱ የጥፋት ኃይሎችን አጀንዳ በማመከን፣ መንግሥት ለጀመረው ሀገረ መንግሥት ግንባታ፣ ለተቋማት ጥንካሬ እና ዘላቂ ሰላም ማረጋገጥ ሒደት ጽኑ ዘብ በመቆም፣ የበለጸገች እና የተከበረች ኢትዮጵያን ወደፊት እያሻገረ ይገኛል። የአሮጌው ዘመን አዙሪት ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ተሰብሯል!
#ኢቢሲ