06/08/2026
የሰሜን አሪ ወረዳና የገሊላ ከተማ አስተዳደር ማህበረሰብን የጤና ችግር የሚያቃልል ዘመናዊ አምቡላንስ ተበረከተ!
ሐምሌ 30/2018ዓም ጂንካ
የአሪ ዞን ጤና መምሪያ ከደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ የተበረከተለትንና ከ7 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የተደረገበትን እጅግ ዘመናዊ አምቡላንስ ለሰሜን አሪ ወረዳ አስረክቧል።
ይህ አምቡላንስ የማህበረሰቡን የጤና መሠረተ ልማት ለማሟላትና በተለይም የእናቶችና ህፃናትን ጤና ለመጠበቅ ትልቅ አቅም እንደሚፈጥር ተገልጿል።
የአምቡላንስ ርክክቡ በተደረገበት ወቅት የዞኑ ከፍተኛ አመራሮች የተገኙ ሲሆን፣ ተሽከርካሪው ወረዳው ላይ ሲደርስም የወረዳው አመራሮችና የአካባቢው ማህበረሰብ ደማቅ አቀባበል አድርገውለታል።
በቁልፍ ርክክብ መርሃ ግብሩ ላይ የአሪ ዞን አስተዳደር ፅህፈት ቤት ኃላፊ አቶ አለማየሁ ሼቺ፣ የዋና አስተዳዳሪ አማካሪ አቶ አማረ ጌታሁን፣ ሌሎች ከፍተኛ አመራሮች እና የጤና መምሪያ የማናጅመንት አባላት በክብር ተገኝተዋል።
የሰሜን አሪ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ጎሳዬ ጉሳር ወረዳው ካለው ርቀት፣ የመሠረተ ልማት ችግርና የተሽከርካሪ እጥረት አኳያ የወረዳውን ማህበረሰብ ችግር አይተው ቅድሚያ ስለሰጡ በወረዳውና በገሊላ ከተማ አስተዳደር ስም ምስጋና አቅርበዋል።
የአሪ ዞን ጤና መምሪያ ኃላፊ አቶ በድሉ ባጊማሶ አምቡላንሱ የተሰጠው ወረዳው ካለው የህዝብ ብዛትና ርቀት አንፃር የአገልግሎት እጥረቱን ታሳቢ በማድረግ መሆኑን ገልጸዋል።
ተሽከርካሪው ከሌሎች በአሠራሩ የተለየና ከፍተኛ ወጪ የወጣበት በመሆኑ ለረጅም ዓመታት እንዲያገለግል በጥንቃቄ መያዝ እንዳለበትም አሳስበዋል።
የአሪ ዞን ሽግግር ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ ክብርት ወ/ሮ ስመኝ ተስፋዬም የዞኑ አስተዳደር ለሰሜን አሪና ለገሊላ ከተማ ቅድሚያ በመስጠቱ አድንቀዋል። አምቡላንሱ በጥቃቅን ምክንያት ሳይበላሽና ሳይቆም፣ በተለይም ለእናቶችና ለህፃናት ህይወት ማዳኛ በአግባቡ በጥንቃቄ እንዲያገለግል መልዕክት አስተላልፈዋል።
የሰሜን አሪ ወረዳ ጤና ፅህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ሲሳይ ጥላዬ ለማህበረሰቡ ጤና፣ በተለይም ለእናቶችና ህፃናት ጥበቃ ልዩ ትኩረት በመስጠቱ የዞኑን ጤና መምሪያና የዞኑን አስተዳደር በላቀ ሁኔታ አመስግነዋል።
ኣዞመኮአ