10/10/2022
መስከረም 30/2015 ዓም
------------------------------
ከመስከረም 30/2015 ዓም የ12ኛ ክፍል ብሄራዊ ፈተና በመላ ሀገሪቱ እየተሠጠ በሚገኝበት ዕለት በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ በደረሰው አደጋ የደ/ብ/ብ/ህ/ክ/መንግስት ትምህርት ቢሮ ማዘኑን ገለጸ፡፡
------------------------------------------------------
በዛሬው ዕለት ጠዋት በሀዋሳ ዩኒቨርስቲ የሚፈተኑ የ12ኛ ክፍል ተፈታኝ ተማሪዎች የዩኒቨርስቲዉን ዋናውን ግቢ እና የቴክኖሎጂ ካምፓስን የሚያገኛኘው ድልድይ በመፍረሱ ምክንያት ድልድዩን ሲሻገሩ በነበሩ ተማሪዎች ላይ በደረሰዉ ጉዳት ማዘኑን የትምህርት ሚኒስቴር በይፋዊ ማኅበራዊ ገጹ ላይ አስፍሯል፡፡
ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ አክሎም ጉዳት የደረሰባቸው ተማሪዎች በሀዋሳ ሪፈራል ሆስፒታል ህክምና እየተደረገላቸዉ እንደሚገኝና የተከሰተውን ሁኔታ መላዉ የሀዋሳ ዩኒቨርስቲ እና የትምህርት ሚኒስቴር ግብረ ሀይል በቅርበት እየተከታተለ በመሆኑ ወላጆች እንዳይደናገጡ አሳውቋል፡፡ ሚኒስቴሩ አያይዞም ጉዳት የደረሰባቸዉ ተማሪዎች በቀጣይ በሚሰጠዉ ፈተና የሚፈተኑ መሆኑን በመግለጽ ሌሎች ተማሪዎች በአጋጣሚዉ ሳይረበሹ ተረጋግተዉ እንዲፈተኑ አሳስቧል፡፡
የደ/ብ/ብ/ህ/ክ/መንግሥት ትምህርት ቢሮም በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ በደረሰው ጉዳት ለተጎዱ አካላት ሀዘኑን እየገለጸ ቢሮው በክልሉ ውስጥ ለሚገኙ ተፈታኝ ተማሪዎች፣ ወላጆች፣ መምህራን፣ የትምህርት አካላት እና መላው ማኅበረሰብ ከሀሰተኛ መረጃዎች በመጠበቅ በየአካባቢያቸው የሚሰጠውን ፈተና በስኬት ለማጠናቀቅ እንዲቻል ትብብር እንዲያደርጉ ያሳስባል፡፡
መረጃው፦ የደቡብ ክልል ትምህርት ቢሮ መንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት