06/09/2026
ለመላው የመንዝ ጌራ ወረዳና አካባቢው ነዋሪዎች በሙሉ መጪውን የጳጉሜ 3 በዓል ለማክበር ከመንዝ ጌራ ምድር ወረዳ ባህል ቱሪዝምና ስፖርት ጽ/ቤት ጥሪ ቀርቧል።
የጽ/ቤቱ ኃላፊ ወ/ሪት ማህሌት የሚከተለውን መልዕክት አስተላልፈዋል።
በመጀመሪያ እንኳን ለ2018 ዓ.ም ጳጉሜ 3 ለሚከበረው ምስአለ ማርያም ደብረ-ሀይል ቅዱስ ሩፋኤል ዓመታዊ ክብረ በዓል በሰላም አደረሳችሁ
ምስሓለ ማርያም ቅዱስ ሩፋኤል ከመሐል ሜዳ በቅርብ ርቀት በተሽከርካሪ በስተምዕራብ በኩል ፀሐይ ሲና ድረስ 13 ኪ.ሜ ተጉዘው ከዋናው መስመር በስተ ደቡብ የ6 ኪ ሜ ርቀት በመኪና ከተጓዙ በኃላ የሚገኝ ቅዱስ ስፍራ ነው ::
ምስሓለ ማርያም ላይ በኢትየጵያ ታሪክ የመካከለኛው ክፍለ ዘመን ነገስታት አሻራቸውን እንዳሳረፉበት ታሪክ ይናገራል ፡፡
የመጀመሪያው አፄ አምደ ፅዮን (1297-1327) ሲሆን በዚህ ቦታ ላይ ቤተ መቅደስ አሰርቶ ቦታውን ምስአለ ማርያም ብሎ መሰየሙ ይነገራል፡፡
ትርጉሙም ማርያምን የምለምንበት ማለት ነው፡፡ በአፄ ይስሀቅ ገብረ መስቀል ዘመነ መንግስት (1414-1429) አባ ጊዮርጊስ የጋስጫው በምስሓለ ማርያም ተቀምጠው ታቦተ ማርያምን እያለገሉ መፅሐፈ ምስጢር የተባለውን መፅሀፍ እንደፃፉም ይነገራል፡፡ መፅሐፉም ጋሞ ጎፉ በርበር ማርያም ቤተክርስቲያን ውስጥ እንደሚገኝ ታውቋል፡፡
አፄ ዘርአ ያእቆብ በ1434-1468 ዘመን ወደ አዳል ሀገር ሲዘምት እድል ከእርሱ ጋር እንዲሆን ምስአለ ማርያምን ተማፅኖ እና ድል አድርጎ ከተመለሰ ቤተ- ክርስቲያን በቦታው ላይ ለማሰራት ስለት ተሳለ፣በዘመቻውም ድል አድርጎ ከተመለሰ በኋላ በቦታው ላይ ቤተ ክርስትያን የማሰራት ውጥኑን ሳያሳካ እንደሞተ ይነገራል፡፡
ነገር ግን በዱካው የተተካው የአፄ ዘርዓያእቆብ ልጅ አፄ በእደ ማርያም (1468-1478) ለዘመቻ በዚህ ቦታ ሲያልፍ ምስአለ ማርያምን አይቶ በቦታው ውበት ተደንቆ በጊዜው የነበሩ አባቶችን የዚህችን ቦታ ታሪክ እንዲያጫውቱት አጥብቆ ይጠይቃቸዋል፡፡
ታሪክ አዋቂ አባቶችም ታቦተ ማርያም በቦታው ላይ እንዳለች ነግረውት አባቱም አፄ ዘርአያዕቆብ ቤተ-ክርስቲያን ለማሰራት የተሳለውን ስለት ሳያሳካ እንደሞተ ያስረዱታል፡፡
በእደ ማሪያም በዚህ ታሪክ እጅግ ይደነቃል፡፡ በኋላም አባቱ የተሳለውን ስለት ብቻም ሳይሆን እርሱም አሁን በሚሄድበት ዘመቻ ላይ ድል ከቀናው ቤተክርስትያኗን እንደሚያሰራ ምስአለ ማርያምን ተማፅኖ ዘምቶ ድል አድርጎ ተመለሰ፡፡
እንዳለውም ቤተክርስቲያኗን አንፆ ሰርቶ ታቦቷን በማስገባት ያባቱንም ቁጭት ተወጣ፣ ለራሱም ለምሰጋና የሚሆን የስለት ስጦታውን ምስአለ ማሪያም አበረከተ፡፡አፄ በእደ ማርያም በዚህ ብቻ አላበቃም በዚያው ባሰራው ቤተክርስትያን አቅራቢያ የራሱን ቤተ- መንግስት አሰርቶ ምስአለ ማሪያምን መናገሻ ከተማው አድርጎ ኖረ፡፡
በዚህም ምክንያት፡- ታቦቱ ልደታ ማርያም ገዢው በእደ ማርያም አቃቢቷ ወ/ማርያም ሀገሩ ምስአለ ማርያም ይባል ነበር፡በተጨማሪም በዩዲት ጉዲት የተሰደዱትን በዋሻ ውስጥ ተቀብረው የቆዩ ክርስትያኖችን ከመርሀ ቤቴ ነጭ ገደል ተብሎ ከሚጠራው አካባቢ አስመጥቶ በዚህ ቦታ ላይ አብረው ተዳብለው እንዲኖሩ አድርጎ ለመተዳደሪያ የሚሆን ሀብት፣ ንብረት እና አልባሳት እንደሰጠ ይነገራል፡፡
በ1988 ከፈረንሳይ የመጡ አርኪዮሎጂስቶች በፊት አውራሪ ገብረ ህይወት (የʻʻአራዳʼʼ መፅሃፍ ደራሲ) አስተባባሪነት በዚህ አካባቢ ላይ በተደረገው 1 አመት የፈጀ ቁፋሮ እና ምርምር የአፄ በእደ ማርያም ቤተ -መንግስት ግምጃ ቤት እና ሌሎች ክፍሎች ፍርስራሾችን ጨምሮ ከሸክላ እና ከተለያዩ ቁሳቁሶች የተሰሩ የመመገቢያና የመገልገያ እቃዎች ተገኝተዋል፡፡
እነዚህም የተገኙት የመገልገያና መመገቢያ መሳሪያዎች አሁን አዲስ አበባ በአራት ኪሎ ብሄራዊ ሙዚየም በቅርስነት ተቀምጠው ይገኛሉ፡፡ ምስአለ ማሪያም በየአመቱ ጳጉሜ 3 ታቦቱ የሚነግስ ሲሆን ይህ በዓል ከድግምሻ ሃምሳ ማረሻ፣ ከገደምቦ ሃምሳ ገንቦ፣ ከአፍተነት ሃምሳ ነት፣ ከቄውላ ሃምሳ ዱላ እየተባለ ሲከበር የኖረ ታሪካዊ በዓል ነው፡፡
በየአመቱ በዚሁ እለትም የሚውል ታሪካዊ የገበያ ስረዓት አለ፡፡ በአፈ ታሪክ እንደሚነገረው በዕለቱ ለገበያ የቀረበ ማንኛውም የገበያ ሸቀጥ እና የቁም እንስሳት ግብይት ላይ ከተወደደ በቀጣዩ አመትም ተወዶ ይቆያል፤ ከረከሰም አመቱን ሙሉ ረክሶ ይውላል እየተባለ የቀጣዩ አመት የገበያና የኑሮ ሁኔታ የሚተነበይበት ነው፡፡
ሌላው በዚህ ዕለት ዝናብ ቢዘንብ ዣን ጥላን ዘርግቶ የሚከለል የለም እንደውም የሚዘንበው ዘናብ በደንብ እንዲመታው ተሰተካክሎ ይቆማል እንጅ ምክንያቱ ደግሞ ይህ ዝናብ በአመት አንድ ጊዜ የሚገኝ ድንቅ ፀበል ሰልሆነ ነው፡፡ በከተማና እራቅ ባለ አካባቢ በሚኖረው ማህበረሰብ ዘንድ ደገሞ ከወዲሁ በዋዜማው ጳጉሜ 2 ለሊት ከዘነበ ፀበል ለማግኘት ሰፋ ያለ እቃ ተደቅኖ ያድራል በተገኘው ፀበልም ቤትና ገቢ ይረጫል ለበረከት ዱቄት በማዘጋጀትም ይቦካል ወዘተ፡፡
ምስአለ ማርያም ላይ ሌላው ለየት ያለው ታቦቱን ለማንገስና አካባቢውን ለመጎብኘት የሄደ ሰው የአካባቢው ተፈጥሯዊ አቀማመጥ እድሜ ጠገብ የጽድ ዛፎች ፣ወይራ ዝግባ እና ሌሎችም ሀገር በቀል ዛፎች ያሉበት በመሆኑ ወደ ውስጥ ሲገቡበት መንፈስን የሚያድስ ጸጥታ ካካባቢው ውጡ ውጡ የማይል ስሜትን ይፈጥራል መንፈስንም ያድሳል፡፡ ከዚህ ባሻገር ቦታው ከ713 አመታትን በላይ ወደ ኋላ የሚመልስ የታሪክ አሻራዎች ያረፉበት ቦታ ነው፡፡ይህ ቦታ ከሀይማኖታዊ ቦታነቱም ባሻገር የቱሪስት መስህብ እንዲሁም የጥናትና የምርምር ቦታ የሆነናበቀጣይ ሰፊ በዘርፉ ሰፊ ስራ ሊሰራበት የሚችል ነው፡፡
ይህ ውብና ማራኪ የሆነ ታሪካዊ፣ባህላዊና ሀይማኖታዊቱውፊቶች የሚከናወኑበት ስፋራ ለወረዳችን ትልቅ የመስህብ ሀብትናመዳረሻ አድርጎ ከመጠቀምና የወረዳችንና የአካባቢው ማህበረሰብ ከቱሪዝም ዘርፍ የሚገኘውን ሁለንተናዊ ጥቅም እንዲያገኝ አልሞ መስራት ይጠይቃል የወረዳው ባህል ቱሪዝምና ስፖርት ፅ/ቤትም በያዝነው ዓመት ይህንን ቅዱስ የሆነ ጥናታዊና ታሪካዊ ስፍራ በቱሪስት መዳረሻነት በመያዝ በዘርፉ የሚታዩትን የመሰረተ ልማት አውታሮች ችግር ከወረዳው መንግስት፣ከአጋርና ባለድርሻ አካላት ጋር ለማሟላት ዕቅድ በመያዝ እየተንቀሳቀሰ ይገኛል፡ ከዚህ አኳያ የመስህብ ስፍራው የተለያዩ የመሰረተ ልማቶችን አልተሟሉለትም በህዝቡና በመንግስት ትብብር የ24 ሰዓት መብራት ተጠቃሚ ሆኗል ይሁን እንጂ ክረምት ከበጋ የሚያስገባ መንገድ፣ የእንግዶች /የእምነት ቱሪስት ማረፊያ፣መጸዳጃ ቤት፣ንፅህ መጠጥ ውሃ አቅርቦት አልተሟላለትም፡፡ በመሆኑም ይንን ቅዱስ፣ጥንታዊና ታሪካዊ የሆነውን ስፍራ እንደወረዳ በማልማት ወረዳችንና ህዘቡ ከቱሪዝም ዘርፉ ማግኘት የሚገባውን ዘርፈ ብዙጥቅም ማግኘት እንዲችሉ ሁላችንም የሚጠበቅብንን ድርሻ ልንወጣ ይገባናል በማለት መልዕክታችንን እናስተላልፋለን፡፡
የመንዝጌራ ምድር ወረዳ ባህል ቱሪዝምና ስፖርት ጽ/ቤት ስ.ቁ0116850600