15/08/2026
በሼይ ቤንች ወረዳ የታቀደውን የገቢ ዕቅድ ለማሳካት በተቀናጀና በባለቤትነት የገቢ ስራን መሥራት እንደሚገባ ተጠየቀ
ነሀሴ 09/2018 (የደምኢህክመ ገቢዎች ቢሮ)
በቤንች ሸኮ ዞን በሼይ ቤንች ወረዳ በበጀት ዓመቱ የታቀደውን የገቢ ዕቅድ በማሳካት የህብረተሰቡን የልማት ጥያቄዎችን ለመፍታት ሁሉንም የገቢ አማራጮችን ለይቶ እና አሟጦ መሰብሰብ ያስፈልጋል ተብሏል።
ይህ የተገለጸው በሼይ ቤንች ወረዳ ከዘርፉ ባለ ድርሻ አካላት ጋር እየተደረገ ባለው የገቢ ስራዎች ውይይት መድረክ ነው።
በውይይቱ የወረዳው ዋና አስተዳዳሪ አቶ ክፍሌ ጎበዜ እንደገለጹት በበጀት ዓመቱ የታቀደውን የገቢ ዕቅድ ለማሳካት በተቀናጀና በባለቤትነት የገቢ ስራን መሥራት ከሁሉም ይጠበቃል ብለዋል።
ዕቅዱን ለማሳካት ሁሉንም የገቢ አማራጮችን ለይቶ እና አሟጦ መሰብሰብ እንደሚገባ ነው ያሳሰቡት።
ፈጣን የልማት ዕድገት ቀጣይነት እንዲኖረው የህብረተሰቡን አዳጊ የልማት ፍላጎቶችን ለማሟላት ገቢን በሚጠበቀው ፍጥነትና ቅልጥፍና መሰብሰብ ይገባል ብለዋል።
የወረዳው ም/ል አስተዳዳሪና ትራንስፖርት ጽህፈትቤት ኃላፊ አቶ ጎበዜ ተሰማ በበኩላቸዉ ኢኮኖሚ የሚያመነጨውን ገቢ አሟጦ ለመሰበሰብ እና መልሶ ለልማት ለማዋል ተግቶ መሥራት ያስፈልጋል ብለዋል።
የመደበኛ የገቢ ስራዎችንና የማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎቶች የገቢ አሰባሰብ ሂደትን ወቅቱ በሚጠይቀው ልክ ማስኬድና ማቀላጠፍ እንደሚገባ ነው ያሳሰቡት።
በወረዳው በ2019 በጀት ዓመት ከሁሉም ገቢ አማራጮች ከ418 ሚልዬን በላይ ገቢ ለመሰበሰብ ታቅዶ እየተሠራ መሆኑ ተገልጸዋል።
ዘገባው የወረዳው የመንግስት ኮምንኬሽን ነው