14/10/2021
የኢትዮጵያ ፖሊስ ዩኒቨርሲቲ ከመካከለኛ አመራር ወደ ከፍተኛ አመራር የማዕረግ ሽግግር እና በማህበረሰብ አቀፍ ፖሊስ አገልግሎት ያሰለጠናቸውን አመራሮችና አባላትን አስመረቀ፡፡
*******************************************************************
ጥቅምት 04/2014ዓ/ም ኢትዮጵያ ፖሊስ ዩኒቨርሲቲ ሰንዳፋ፤
የኢትዮጵያ ፖሊስ ዩኒቨርሲቲ በረጃጅምና በአጫጭር ትምህርትና ስልጠናዎች በመስጠት የዜጎችን ሰላምና ደህንነት መጠበቅና ማስጠበቅ የሚችሉ የፖሊስ አመራሮችና አባላትን በማስተመርና በማሰልጠን የ75 ዓመት ዕድሜ ያለው አንጋፋ የትምህርትና ስልጠና ተቋም ነው፡፡ዩኒቨርሲቲው በዛሬው ዕለት የፌደራል ፖሊስ አባላት መተዳደሪያ ደንብ ቁጥር 268/2005ዓ.ም አንቀፅ 13 ንዑስ ቁጥር 2/ለ ከኢንፔክተር ወደ ዋና ኢንስፔክተር የሚደረግ የማዕረግ እድገት በውድድር፣በፈተና እና በስልጠና በሚለው መሰረት በጥር 2012ዓ/ም እና በሐምሌ 2012ዓ/ም የቆይታ ጊዜያቸውን ላጠናቀቁ 117 ኢንስፔክተሮች በዩኒቨርሲቲው ለ 3 ተከታታይ ወራት የተሠጠውን ስልጠና በሚገባ በማጠናቀቃቸው ዋ/ኢ/ር ማዕረግ ያገኙ ሲሆን ከዚህ ባሻ ገር በዩኒቨርሲቲው ለ15 ተከታታይ ቀናት የማህበረሰብ አቀፍ ፖሊስ አገልግሎት ስልጠና ሲከታተሉ የቆዩ 98 አመራሮችና አባላት ተመርቀዋል፡፡
በምርቃት ስነ-ስርዓቱ ላይ በመገኘት ንግግር ያደረጉት በኢ/ፖ/ዩ የፖሊሳዊ ስልጠና ፣አካል ብቃት፣አጫጭር ስልጠናዎች ም/ፕሬዚዳንት ምክትል ኮሚሽነር ጋሹ አለማየሁ ከአንድ ማዕረግ እርከን ወደ ሌላኛው የማዕረግ እርከን ስትሻገሩ ከፍተኛ ሀላፊነት የተጣለባችሁ በመሆኑ በዛሬው ዕለት ከመካከለኛ አመራር ወደ ከፍተኛ አመራር የተሸጋገራችሁ መኮንኖች ለቀጣይ ተልዕኮ የምትዘጋጁበት በመሆኑ ጠንክራችሁ መስራት አለባችሁ ሲሉ የገለፁ ሲሆን በዚህም አያይዘው በማህበረሰብ አቀፍ ፖሊስ አገልግሎት ሰራ ላይ የተሰማችሁና በዩኒቨርሲቲያችን ገብታችሁ ያገኛችሁትን ዕውቀት በተጨባጭ እንድትተገብሩ ሲሉ አመላክተዋል፡፡
በመጨረሻም የኢትዮጵያ ፖሊስ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ምክትል ኮሚሽነር ጀነራል መስፍን አበበ ስልጠና ለአንድ ተቋም በራሱ ግብ ሳይሆን ከስልጠናው በኋላ የታሰበለትን ዓለማ ሊያሳካ የሚችል የተግባር እና የአስተሳሰብ ለውጥ ማምጣት የሚችል የሰው ሀይል ማፍራት ነው ያሉ ሲሆን ለሁሉም ተመራቂዎች የሥራ መመሪያ ሠጥተዋል፡፡