18/08/2026
ከኢፌዴሪ ትምህርትና ሥልጠና ባለሥልጣን የተውጣጣ ልዑክ በኮሌጃችን የግንዛቤ ማሰጨበጫ ሥልጠና እየሰጠ ነው::
ወ/ሶ/ግ/ኮ ነሐሴ 12/2018 ዓ/ም
ከኢፌዴሪ ትምህርትና ሥልጠና ባለሥልጣን የተውጣጣ ልዑክ በኮሌጃችን በመገኘት የመጀመሪያ ዲግሪ፣ ሁለተኛ ዲግሪና ሦስተኛ ዲግሪ መርሐ-ግብሮች ፈቃድ አሰጣጥና ዕድሳት መገምገሚያ መስፈርቶችን በተመለከተ ለሚመለከታቸው የሥራ ክፍል ኃላፊዎች የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥልጠና እየሰጠ ይገኛል።
መድረኩን በንግግር የከፈቱት የኮሌጃችን ትምህርትና ሥልጠና ዘርፍ ኃላፊና ምክትል ዲን አቶ ታሪኩ ጨመረ፣ የመጀመሪያ ዲግሪ መርሐ-ግብር ትምህርት መጀመር ለተቋማችንና ለባለድርሻ አካላት የረጅም ጊዜ ጥያቄ ሆኖ መቆየቱን አውስተው፤ መርሐ-ግብሩን ለመጀመር የሚያስችሉ የቅድመ-ዝግጅት ሥራዎች ተጠናቀው በመጨረሻ ምዕራፍ ላይ መድረሳቸውንም ገልጸዋል።
አቶ ታሪኩ አክለውም፣ ወቅቱ ለተቋማችን ወርቃማ መሆኑን በመጠቆም፣ ሠልጣኞች ሥልጠናውን በትኩረት በመከታተል ለህደቱ ስኬታማነት ድርሻቸውን በአግባቡ እንዲወጡ አሳስበዋል።
በባለሥልጣኑ የከፍተኛ ትምህርት ፈቃድ አሰጣጥ ባለሙያ አቶ መንግሥቱ ጠና እንደገለጹት፣ ባለሥልጣኑ “ጥራት ያለው ትምህርት ለሁሉም” በሚል መሪ ቃል በትምህርት ጥራት ላይ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ ይገኛል።
ሥልጠናው ዛሬን ጨምሮ ለሁለት ተከታታይ ቀናት እንደሚቆይ የተገለጸ ሲሆን፣ ሥልጠናው ከተጠናቀቀ በኋላ ልዑኩ የመጀመሪያ ዲግሪ መርሐ-ግብር ለመጀመር ከሚያስችሉ መስፈርቶች አንፃር የኮሌጁ ቅድመ ዝግጅት ሥራዎች እንደሚገመገሙ ተጠቅሷል።
በግምገማውም ተቋማችን በመርሐ-ግብሩ ተማሪዎችን ተቀብሎ ለማስተማር የሚያስችሉ የሰነድ ዝግጅቶችንና ግብዓቶችን በመስክ ምልከታ እንደሚገመግም ተገልጿል።
በመድረኩ ላይ ከባለሥልጣኑ የተውጣጡ አሰልጣኞች፣ የኮሌጃችን ትምህርትና ሥልጠና ዘርፍ ኃላፊና ምክትል ዲን አቶ ታሪኩ ጨመረ፣ የኮሌጃችን አስተዳደርና ልማት ዘርፍ ኃላፊና ምክትል ዲን አቶ አበባየሁ መንኤና ሌሎች አካዳሚክ ኮሚሽን አባላትና የመጀመሪያ ዲግሪ መርሐ-ግብር የቅድመ-ዝግጅት ሥራ ኮሚቴ አባላትን ጨምሮ ሌሎች አመራሮችና ሠራተኞች እየተሳተፉ ይገኛሉ።