30/08/2026
በካራት ከተማ ለምለም ሰፈር የተከሰተ ድንገተኛ የእሳት አደጋ በንብረት ላይ ከፍተኛ ጉዳት አደረሰ
በኮንሶ ዞን ካራት ከተማ ለምለም ሰፈር ዛሬ ከጠዋቱ 4፡00 ሰዓት አካባቢ የተከሰተ ድንገተኛ የእሳት አደጋ በሱቆች፣ በሆቴሎችና በመኖሪያ ቤቶች ላይ ከፍተኛ የንብረት ጉዳት አድርሷል።
በአደጋው ከጅንካ፣ ያቤሎ፣ አርባምንጭና ከሌሎች አጎራባች ከተሞች የሚመላለሱ መንገደኞችን በየዕለቱ ያስተናግድ የነበረው ማሙሽ ደጉ ሆቴል ከባድ ጉዳት ደርሶበታል።
እሳቱ የተነሳው ከቀኑ 4፡00 ሰዓት አካባቢ እና ዕለቱም ዕሁድ በመሆኑ፣ አብዛኛው ሰው ወደ መኖሪያ ቤቱ በመሄዱ የእሳቱን መቆጣጠርና ማጥፋት ሥራ ፈታኝ እንዲሆን አድርጎታል።
የካራት ከተማ ከንቲባ አቶ ጋሻው ኩሲያ እንደገለጹት፣ ጠንካራ የእሳት ማጥፋት ልምድ ያለው የኮንሶ ሕዝብ ከከተማው ማዕከልና ከአቅራቢያው ሰፈሮች በመረባረብ በእሳቱ ሊደርስ የነበረውን ሰፊ ጉዳት መቀነስ ችሏል።
ከንቲባው አክለውም፣ እሳቱን ለመቆጣጠርና ለማጥፋት በከተማው የሚገኙ የፌዴራል ፖሊስና የከተማው ህብረተሰብ ያደረጉት በሙያ የታገዘ ርብርብ የሚደነቅ መሆኑን ገልጸው፣ በተለይም የከተማው ሕዝብ ያደረገውን ብርቱ ርብርብ አድንቀዋል።
የአደጋው መንስኤና በንብረት ላይ የደረሰው ጉዳት መጠን በሚመለከተው አካል እየተጣራ ሲሆን፣ የተሟላ መረጃ ሲደርስ ለሕዝብ የሚቀርብ ይሆናል።
በኮንሶ ሕዝብ ዘንድ ከእሳት አደጋ መከሰት በኋላ ተጎጂዎችን በመደገፍና በመጽናናት የሚታወቀው ማኅበራዊ ባህል እንዳለ የሚታወቅ ሲሆን፣ በቀጣይም ተጎጂዎችን ለመደገፍና የደረሰባቸውን ጉዳት ለማቃለል የሚደረገው የጋራ ርብርብ እንደሚጠናከር ይጠበቃል።
ዘገባዉ የኮንሶ ዞን ኮሙኒኬሽን ነዉ