28/08/2026
የወላይታ ብሔር ባህላዊ የዘመን መለወጫ ክብረ በዓል “ጊፋታ” አከባበር ቅድመ ዝግጅት ሥራዎችን የክልሉ ባህልና ስፖርት ቢሮ ድጋፋዊ ክትትል አድርጓል
ወላይታ ሶዶ: ነሐሴ 22/2018 ዓ.ም
በተባበሩት መንግስታት ትምህርት፣ ሳይንስና ባህል ድርጅት (ዩኔስኮ) በሰው ልጆች ወካይ ቅርስነት የተመዘገበው የወላይታ ብሔረሰብ ባህላዊ የዘመን መለወጫ ክብረ በዓል“ጊፋታ” አከባበር ቅድመ ዝግጅትን አስመልክቶ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ባህልና ስፖርት ቢሮ የባህል ልማት ዘርፍ የተደራጀ ድጋፋዊ ክትትል አድርጓል።
የቢሮው ምክትል እና የባህል ልማት ዘርፍ ኃላፊ አቶ ታሪኩ ኦይቻ የተመራው የቢሮ የባህል እሴቶችና ብዝሃ-ባህል ሀብቶች ጥናት ጥበቃና ልማት ዳይሬክቶሬት ከፍተኛ ባለሙያዎች በወላይታ ዞን ሶዶ ከተማ ተገኝተው ከዞኑ ባህልና ስፖርት መምሪያ ኃላፊና የማኔጅመንት አባላት ጋር ተወያይተዋል።
የቢሮው የባህል እሴቶችና ብዝሃ-ባህል ሀብቶች ጥናት ጥበቃና ልማት ዳይሬክቶሬት ከፍተኛ ባለሙያዎች በድጋፍና ክትትል ወቅት በቅድመ-በዓሉ ዝጅት የሚከናወኑ ባህላዊ የእርቅና የሽምግልና ስርዓቶችን፣ የእደጥበብ ውጤቶችን፣ የባህላዊ ምግብና መጠጥ፣ ባህላዊ መድኃኒት እንዲሁም የአገር በቀል ዕውቀቶች እና የኪነጥበብ ሥራዎች በዕቅድ እስከ ታችኛው መዋቅር እየተሰሩ መሆናቸውን በመስክ ምልከታው ማየት ችለዋል።
በተጨማሪም የብዝሃ-ባህል ሀብቶች፣ የሀገረሰብ ባህልና ቱባ ባህላዊ እሴቶችን ለማልማት በተደራጀ መልኩ ለኤግዝቪሽን መዘጋጀቱንና በዕቅድ እየተመራ መሆኑን የክትትል ቡድኑ ተመልክቷል።
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ባህልና ስፖርት ቢሮ ም/ቢሮ ኃላፊና የባህል ልማት ዘርፍ አቶ ታሪኩ ኦይቻ ክብረ በዓሉ ለአብሮነት፣ ለዘላቂ ሰላም፣ ለህዝብ ትስስርና የፍቅር የመተባበር በዓል እንድሆንና ያልተበረዘ በቀድምት ባህላዊ ሥርዓት መከተል እንዳለበት በአፅንኦት አሳስበዋል ።
አያይዘውም የወላይታ ብሔረሰብ የዘመን መለወጫ “ጊፋታ” የክልሉ ብቻ ሳይሆን የሀገርና የዓለም ሀብት ሆኖ የተመዘገበ በመሆኑ የበዓሉ ዓከባበር ከቅድመ ዝግጅቱ ጀምሮ የሚከውኑ የክብረ በዓሉ ኩኔቶች በተደራጀ መልኩ ቱባ ባህሉን በጠበቀ መልኩ ለትውልድ እንዲተላለፍ በትኩረት መሠራቱ እንዲጠናከር አሳስበዋል ።
የወላይታ ዞን ባህልና ስፖርት መምሪያ ኃላፊ፤ የወላይታ ሶዶ ከተማ አስተዳደር ባህልና ስፖርት መምሪያ ኃላፊ እና የሁለቱ መዋቅሮች የማኔጅመንት አባላት በተገኙበት ነው ውይይቱ የተደረገው።
/