03/09/2026
"የስፖርት ዘርፉን በባህላዊ አሠራር ብቻ መምራት አይቻልም" አብዱ ሁሴን (ዶ/ር)
የስፖርት ዘርፉን ከዚህ በፊት በነበረው ባህላዊ አስተሳሰብና አሠራር ብቻ መምራት የሚቻልበት ወቅት አለመሆኑን የአማራ ክልል ም/ርዕሰ መስተዳድርና የክልሉ ስፖርት ምክር ቤት ሰብሳቢ ዶ/ር አብዱ ሁሴን ገለጹ።
ዶ/ር አብዱ ሁሴን ይህን የገለጹት 27ኛው የአማራ ክልል ስፖርት ምክር ቤት ጉባኤ በባህር ዳር ከተማ ሲካሄድ ባስተላለፉት መልዕክት ነው።
ስፖርት ከጤናና ከዜጎች መሠረታዊ መብት ባሻገር ለማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች መፍትሔ የሚያበረክት ዘርፍ መሆኑን ጠቁመው፣ በተለይም ወጣቶችን ተሳታፊና ተጠቃሚ ለማድረግ በየደረጃው ዘመናዊ አሠራር መዘርጋት እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
የክልሉን ስፖርተኞችና አሠልጣኞች ከስፖርቱ የሚገኘውን ዘመናዊ ጥቅም እንዲያገኙ ከማድረግ ባሻገር፣ የክልሉን ተወዳዳሪነት በማሳደግ ለኢትዮጵያ የሚኖረውን አስተዋጽኦ ማሳደግ ከስፖርት አመራሩ የሚጠበቅ ታሪካዊ ኃላፊነት መሆኑንም ገልጸዋል።
በተጨማሪም መንግሥት ለስፖርቱ ዘርፍ ልዩ ትኩረት እየሰጠ መሆኑን ጠቁመው፣ የስፖርት ልማትና አስተዳደር አዋጅ መጽደቅ፣ የስፖርት ፖሊሲ በአዲስ መልክ መዘጋጀትና የስፖርት መሠረተ ልማቶች መገንባት ለዘርፉ እድገት የሚያበረክቱ ተግባራት መሆናቸውን አንስተዋል።
በጉባኤው የ2018 ዓ.ም የሥራ አፈጻጸም፣ የ2019 ዓ.ም ዕቅድና የማስፈጸሚያ በጀት እንዲሁም የ2018 ዓ.ም የኦዲት ሪፖርት በጥልቀት እንደሚገመገም ተገልጿል።