29/08/2026
በእውቀትና በስነምግባር የታንጸ ተወዳዳሪ ትውልድ ለማፍራት ዘመኑን የሚዋጅና የሚመጥን ትምህርት ቤት መገንባት ፋይዳው ከፍተኛ ነው:-ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር )
ነሐሴ 23/2018(ወልቂጤ)በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በጉራጌ ዞን የጉንችሬ ብራይት ቅድመ 1ኛ እና 1ኛ ደረጃ ት/ቤት በዛሬው እለት ተመርቆ ለአገልግሎት በቅቷል።
የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር ) በምረቃ መርሐ ግብሩ ላይ ባስተላለፉት መልዕክት እንደገለጹት ጥራት ያለው ትምህርት ተደራሽ በማድረግ ብቁ፣ በስነ ምግባር የታነጸ ትውልድ እንዲፈጠር በልዩ ትኩረት መስራት ይገባል ብለዋል።
ትምህርት ቤቱ ተገንብቶ ለውጤት እንዲበቃ ላደረጉ ለሚስተር ሮቤርቶ ቤተሰቦች እና ካንትሪ ዳይሬክተር ሆነው እየሰሩ ላሉ አካላት ምስጋና አቅርበዋል።
የትኛውም ፕሮጀክት የሚነሳው ከሀሳብ ነው ያሉት ርዕሰ መስተዳድሩ ሀሳብን ወደ ተግባር በመተርጎም ፕሮጀክቱን እውን ላደረጉ ሁሉ ርዕሰ መስተዳድሩ በራሳቸው እና በክልሉ መንግስት ስም ምስጋና አቅርበዋል።
በኢትዮጵያ የልማት ስራ ተጀመረ እንጂ አዳጊ የሆነውን የህዝብ ፍላጎትን በማሟላት ረገድ ቀሪ ስራ ይኖራል ያሉት ርዕሰ መስተዳድሩ በቀጥተኛ የልማት ስራ መሳተፍ ከጀመረች ጥቂት ዓመታት መቆጠራቸውን ጠቅሰዋል።
የአካባቢው ተወላጆች ተባብረን የልጆቻችንን የወደፊት ብሩህ ተስፋ ማለምለም ይገባል ብለዋል።
የዚህ ዘመን ትውልድ በአለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳዳሪ መሆንን ይሻል ያሉት ርዕሰ መስተዳድሩ ለዚህም ዘመኑን የሚመጥን እና የሚዋጅ ስራ ይጠይቃል ብለዋል።
ትምህርት አለምን የሚለውጥ መሳሪያ ነው ያሉት ርዕሰ መስተዳድሩ ህጻናት ተገቢውን እንክብካቤ አግኝተው ማደግ እንዲችሉ በልዩ ትኩረት መስራት እንደሚገባም አሳስበዋል።
ተያይዘን ኢትዮጵያን እና ክልላችንን እንገነባለን ያሉት ርዕሰ መስተዳድሩ የኢትዮጵያን ትንሳኤ እውን እናደርጋለን ሲሉም ጠቅሰዋል።
ከትምህርት ቤት ግንባታ ባለፈ በጤናውም ዘርፍ የህዝብ ተጠቃሚነት ለማሳደግ የተጀመረው ጥረት ተጠናክሮ መቀጠሉን ተናግረዋል።
በኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ጠቅላይ መምሪያ አዛዥ ምክትል ኮሚሽነር ጀነራል እርስቱ ይርዳው በዚሁ ጊዜ እንደገለጹት መጀመሪያ መዋዕለ እጻናት መገንባት ታሳቢ ያደረገ እንደነበር የተናገሩት
መንግስት የህዝቡን የመሰረተ ልማት ፍላጎት ለማሟላት በልዩ ትኩረት እየተሰራ ስለመሆኑም ምክትል ኮሚሽነር ጀነራሉ
አመላክተዋል።
የአካባቢው ነዋሪዎች በተለይም ወጣቶች የህጻናት ትምህርት ቤት እንዲገነባላቸው ያቀረቡትን ጥያቄ በልበ ቀናነት በመቀበል ወደ ተግባር በመገባቱ ለውጤት በቅቷል ብለዋል።
በከተማው ቅድመ 1ኛ እና አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶችን በመገንባት በዛሬው እለት ለምረቃ ማብቃት መቻሉን ጠቅሰዋል።
ትምህርት ቤቱ አሁን ለደረሰበት ደረጃ እንዲበቃ ዲዛይን ከመንደፍ ጀምሮ የፋይናንስ ድጋፍ በማድረግ የቼንትሮ ኢትዮጵያ መስራች እና ፕሬዝዳንት ለነበሩት ሮቤርቶ ራባቴኒ ምክትል ኮሚሽነር ጀነራሉ ምስጋና አቅርበዋል።
ዛሬ እኒህ ልበ ቀና አባት በህይወት ባይኖሩም ህያው ስራቸው በትውልዱ ዘንድ ሲታወስ እንደሚኖርም ጠቁመዋል።
ከነባር ይዞታቸው ተነስተው ለትምህርት ቤት ግንባታ እንዲሆን ትብብራቸውን ለገለጹ ነዋሪዎች እና ለወንድም ተስፋዬ ይገዙ ምስጋና አቅርበዋል።
የመደመር መንግስት ለህብረተሰቡ ዘርፈ ብዙ የልማት ስራዎችን እያበረከተ ይገኛል ያሉት ምክትል ኮሚሽነር ጀነራሉ ዛሬ የትምህርት እና የጤና ፕሮጀክቶችን አስመረቅን እንጂ ከዚህ በላቀ ደረጃ በሁሉም አካባቢዎች የልማት ስራዎችን ተደራሽ እየተደረገ ስለመሆኑም ጠቅሰዋል።
በከተማም ሆነ በገጠር አካባቢዎች የህብረተሰቡን ህይወት ለማሻሻል የጋራ ትብብር እና ጥረት ይጠይቃል ሲሉም ኮሚሽነር ጀነራሉ ጥሪ አቅርበዋል።
የጉራጌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ላጫ ጋሩማ በበኩላቸው ትምህርት የሁሉም ነገር መሰረት በመሆኑ ሁሉም በዘርፉ ኢንቨስት ሊያደርግ ይገባል ብለዋል።
በዞኑ የትምህርት ጥራትና የተማሪዎች ውጤት ለማሻሻል የትምህርት ቤቶችን ደረጃ የማሻሻል ስራ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል።
እንደ አቶ ላጫ ጋሩማ ገለጻ የዞኑ መንግስት በዘርፉ ውጤት ለማስመዝገብ ለቅድመ መደበኛ ትምህርት ቤት ልዩ ትኩረት በመስጠት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል።
በከተማው የተገነባው ቅድመ አንደኛና አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት በዞኑ ግንባር ቀደምና አርአያነት ያለው መሆኑን ጠቅሰው፤ ይህ ደረጃውን የጠበቀው ትምህርት ቤት በእውቀት የበለጸገ ተወዳዳሪ ትውልድ በማፍራት ረገድ ፋይዳው ከፍተኛ ነው ያሉት።
የኢፌዲሪ መስኖ እና ቆላማ አካባቢ ሚኒስትር ዴኤታ እና የትምህርት ቤቱ ግንባታ አስተባባሪ አቶ ተስፋዬ ይገዙ እንደገለጹት በአካባቢና በሰፈር ሳንታጠር መስራት ከቻልን የህዝባችንን ህይወት መለወጥ ቀላል ነው ብለዋል።
በእርሳቸው አስተባባሪነት በተለያዩ አካባቢዎች 30 ትምህርት ቤቶችን ማስገንባት ችለናል ያሉት አቶ ተስፋዬ በትምህርት ዘርፍ የሚደረገው ኢንቬስትመንት ድንበር የለውም ብሲሉም ጠቁመዋል።
የጉንችሬ ከተማ ከንቲባ አቶ አብድልቋድር ሂጅራ የተማሪዎች ውጤት ለማሻሻል የትምህርት ተቋማት ደረጃቸው ማሻሻል ወሳኝ ነው ብለዋል።
በቀጣይም በዘርፉ የተጀመረውን የትምህርት ጥራትና የተማሪዎች ውጤት ለማሻሻል የሁሉም ባለድርሻ አካላት ርብርብ ማድረግ ይኖርበታል ብለዋል።
የቼንትሮ አዩቲ ፔርሌ የኢትዮጵያ ፕሬዝዳንት ፖውላ አሪቼ እንዳሉት ትምህርት የህጻናትን የወደፊት ህይወት የሚለውጥ መሳሪያ ነው ብለዋል።
በዞኑ የተገነባው ትምህርት ቤት ሀገር የሚለውጡ ዜጎች የሚፈጠሩበት ስለመሆኑም ጠቅሰዋል።
ትምህርት ቤቱ ቀጣይነት እንዲኖረው መሰረተ ልማቱን መጠበቅና መንከባከብ ተገቢ ስለመሆኑም አመላክተዋል።