09/07/2020
‹‹ ዘመን ይግጠምህ ወቅት አይጣልህ፣ የለፋህበትን የምትበላ ፣ለጎደለበት የምትሞላ ያድርግህ . . . ›› ይላሉ አበው ሲመርቁ፡፡ በርግጥም ሰማይ ሳይጨክን ከዘነበ ፣ምድር በወቅቱ ከረጠበ ለኛ ለኢትዩጵያውያን ታላቅ ጸጋ ነው፡፡ ያም አለ ይህ በዝናብ ላይ ለተመሰረተው ግብርናችን ወቅቱ የተስተካከለ በመሆኑና የግብዓትና ቴክኖሎጅ አጠቃቀሙ የተሻለ ለሆነው ደቡብ ወሎ ጃማ ወረዳ የዘንድሮውን የመኸር አዝመራ የተለየና ያማረ እንዲሆን አስችሎታል፡፡
ከደቡብ ወሎ ዞን 20 የገጠር ወረዳዎች አንዱ በሆነው የጃማ ወረዳ 60 ከመቶ አካባቢው ሜዳማ መልክዓ ምድር ይሰፍናል፡፡ ከ63 ከመቶ ለሚልቀው ጥቁር አፈርን ላደለው ለዚህ ወረዳ በስንዴ አምራችነቱ የዞኑ ቁንጮም ነው፡፡ እንኳንስ በእግርና በመኪና እንዳሞራ ክንፍ አውጥተው ቢበሩ የሚያልቅ የማይመስለው የጅባትን ለጥ ያለ ሜዳ ጨምሮ የጃማ መሬት አረንገዴ ሥጋጃን የለበሰ መስሏል፡፡ የምድሩ ልምላሜ፣ የአዝመራው ማማር ከመኪና ይልቅ በእግር መሄድን ያስመርጣል፡፡
ዛሬ ላወጋ የወደድኩት ስለ ጃሞች አዝመራ ሳይሆን በዋና ከተማቸው ደጎሎ እየዘመረ ስላለው የኢንቨስትመንት አዝመራ ነው፡፡ ከጥቂት ዓመት በፊት አንዳች ያልነበራት ጃማ ዛሬ በልጆቿና በልማት አጋሮቿ የላቀ ጥረት እጅግ ይበል የሚያሰኝ ፈጣን የለውጥ ጉዞ ላይ መሆኗን ታዝቢያለሁ፡፡ በደጎሎ ኮሜርሻል (ደጎሎ ዱቄት ፋብሪካ) ፈኗ የተገለጠው የጃማዋ መዲና ደጎሎ ዛሬ አይነ ግቡ ምርጥ የከተማ ቅርጽ እየያዘች ፈጣን ዕድገትን አቀላጥፋ ገፍታበታለች፡፡
አራት ባንኮች ሥራ ላይ ናቸው ኢ.ን.ባ፣ አባይ ባንክ፣ ዳሽን ባንክና አቢሲኒያ ባንክ፣ ፋና ወጊው ግራቪቲ ባለ ኮከብ ሆቴልን ጨምሮ በርከት ያሉ ሆቴሎችና ልዩ ልዩ የንግድ እንቅስቃሴ የሚከናወንባቸው ፎቆች ግንባታቸው እየተቀላጠፈ ይገኛል፣ ዘመናዊ የነዳጅ ማደያም ተጠናቆ ሥራ ሊጀምር ጫፍ ደርሷል፣ በሰዎች ለሰዎች ድርጅት ከ70 ሚሊዮን ብር በላይ ወጭ የሚገነባው ቴክኒክና ሙያ ኮሌጅም እንዲሁ ግንባታው እየተፋጠነ ይገኛል፣ ኮብል ስቶንን ጨምሮ የውስጥ ለውስጥ መንገድና የከተማ ማስፋፋት ሥራው ተጠናክሮ ቀጥሏል፡፡
ጃማ ደጎሎ ፈጣን ዕድገት ላይ ናት ኑ ፊታችሁን ወደ ደጎሎ አዙሩ !! ለአዲስ አበባም ሆነ ለደሴ ቅርብ መሆኗ፣ ከአለም ከተማ ደጎሎ፣ ከደጎሎ ከላላ፣ ከደጎሎ ወረኢሉ ጉጉፍቱ የአስፓልት መንገድ እየተገነባ መሆኑ፣ ተስማሚና ምቹ የአየር ጸባይ ባለቤትነቷ ከሰዎቹ እንግዳ ተቀባይነት ጋር ተደማምሮ ጃማ (ደጎሎን) ተመራጭ የኢንቨስትመንት መዳረሻ አድርጓታልና ገባ ገባ በሉ፡፡ ሲፈልጉ ጣት በሚያስቆረጥመው የበግ ሥጋ ችስቻሶ አንጀት አርሶ፣ ወጥ የት አባቱ ከሚያሰኘው ዝንፍልፍል ነጭ ጤፍ እንጀራዋን በልተው፣ አልያም መሬቷ ካበቀለው ግሩም ስንዴ ዳቦዋን ገምጠው፣ ገንፎዋን በንጹህ ቅቤዋ ያለስስት አወራርደው በሠላም፣ በጤና፣ በፍቅር ከሚኖሩባት ምድር ኑ አብረን እንደግ፣ ኑ አብረን እናልማ የጃማ/ደጎሎ ጥሪ ነው!!